††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን። †††
††† ጥቅምት 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት †††
+" ቅዱስ ጊዮርጊስ ሐዲስ "+
††† ሰማዕቱ የተወለደው በምድረ ግብጽ አሕዛብ (ተንባላት) በሰለጠኑበት የመጀመሪያው ዘመን ነበር:: በተለይ ተንባላቱ ግብፅና ሶርያን ከያዙ በኋላ ባልተጠበቀ ፍጥነት በኃይልም በሰውም ተደራጅተው ነበር:: ቅዱስ ጊዮርጊስ (ልብ በሉልኝ ሊቀ ሰማዕታት አይደለም) የተወለደው በዚህ አስቸጋሪ ጊዜ ነበር::
+እናቱ የተመሠከረላት ክርስቲያን ብትሆንም እንዳለመታደል አባቱ ተንባላታዊ (አሕዛብ) ነበር:: ስሙንም መዛሕዝም ይሉታል:: ሕጻኑ እንደተወለደ ያወጡለት ስም አሕዛባዊ ከመሆኑ ባለፈ በሰዓቱ መጠመቅ አልቻለም:: የወቅቱ ሕግ ከወላጆቹ አንዱ አሕዛባዊ ከሆነና አጠምቃለሁ ቢባል የሚከተለው ሰይፍ ነበር:: በዚሕ ምክንያት ሳይጠመቅ 7 ዓመት ሞላው::
+እናቱ ግን ሕጻን ቢሆንም ፍቅረ ክርስትናን ታስተምረው ነበር:: ባይጠመቅም ጸበሉን: እመነቱን ትቀባው ነበር:: ደብቃ ቅዳሴ ታሰማውም ነበር:: አንድ ቀን ግን ሕጻናት ሲቆርቡ አይቶ ካልቆረብኩ ብሎ አለቀሰ:: ምን ታድርገው? ወደ ውጪ አውጥታ ከአውሎግያ (የሰንበት በረከት) አበላችው:: "ጌታየ! ልጄን እርዳው" አለች::
+ልክ በአፉ ሲቀምሳት መዓዛ መንፈስ ቅዱስ አደረበትና ፍጹም ተደሰተ:: ትንሽ ከፍ ሲል ለምን እንደማይጠመቅና እንደማይቆርብ እናቱን ጠየቃት:: "ልጄ ሆይ! ይገድሉሃል" አለችው::
ከዚህች ቀን ጀምሮ የሚጠመቅበትን ዘዴ ይፈልግ ጀመር::
+አስቀድሞ ትምሕርተ ክርስትናን ተማረ:: ለአካለ መጠን ሲደርስ አፈላልጐ ጠንካራ ክርስቲያን የሆነች ሴት አገባ:: ጥቂት ጊዜ ከቆየ በኋላ ሚስቱን ስለ መጠመቅ አማከራት:: "ሌላ ሃገር ሒደህ ተጠመቅ" አለችው:: ከግብፅ ተነስቶ ሶርያ ገባ::
አባቶችን አፈላልጎ ተጠመቀ:: ቀጥሎም መንገዱን ወደ ልዳ አደረገ::
+ወደ ደብሩ ተጠግቶ አባቶችን "ስም አውጡልኝ" ቢላቸው መንፈስ ቅዱስ አናግሯቸው "ጊዮርጊስ" አሉት:: እሱም ደስ እያለው: ባጭር ታጥቆ የልዳውን ቅዱስ ጊዮርጊስ ያገለግለው ገባ:: ትንሽ ቆይቶ ሁከት መንፈሳዊ ተሰማው:: ማለትም ስለ ሃይማኖቱ ደሙን ማፍሰስ ፈለገና ወደ ግብፅ ተመለሰ::
+በዚያ ያሉ አሕዛብ በክርስትና ስም: ልብስና ሞገስ ሲመለከቱት ተበሳጩ:: ዕለቱኑ አሠሩት:: ሌሊት እናቱና ሚስቱ መጥተው አሉት:- "አደራ! ፍቅረ ዓለም እንዳያታልልህ:: ሰማዕት ብትሆን ላንተም ክብር: ለእኛም ሞገስ ነው" ብለውም አጽናኑት:: እንዲህ ያሉ እናትና ሚስት ማግኘትም ታላቅ እድል ነው::
+ሐዲስ ጊዮርጊስም ጸና:: ከዚያች ቀን ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት ደበደቡት: አካሉን ቆራረጡት: ደሙንም መሬት ላይ አንጠፈጠፉት:: በየመንገዱ እየጎተቱ ተሳለቁበት:: እርሱ ግን ክርስቶስን ወዷልና ሁሉን ታገሰ:: ሌሊት በሆነ ጊዜም ጌታችን ተገልጦ "ከሰማዕታት ተቆጠርህ" አለው::
+በማግስቱ በአደባባይ አንገቱን በሰይፍ ቆረጡት:: ክፋታቸው የጸና ነውና ሥጋውን በእሳት አቃጠሉት:: ወደ ባሕርም ጣሉት:: እናቱ ከባሕር ስታወጣው ግን ምንም አላገኘውም ነበር:: በዚሕች ቀን እናቱና ሚስቱ በክብር ቀብረውታል::
+" አባ ስምዖን ሊቀ ዻዻሳት "+
+በምድረ ግብጽ ተነስተው: በማርቆስ ወንጌላዊ መንበር ላይ ይቀመጡ ዘንድ ከተገባቸው ሊቃነ ዻዻሳት አንዱ እኒህ አባት ናቸው:: ከልጅነታቸው መንነው ብዙ ዘመናትን በተጋድሎ በማሳለፋቸው ሥጋዊ አካላቸው ደካማ ሆኖ ነበር::
+ከገዳማዊ አገልግሎታቸው ቀጥሎም ከእርሳቸው በፊት ለነበሩ ሁለት ፓትሪያርኮች ረዳት ሆነው አገልግለዋል:: በዚህ ጊዜም ለመንጋው የሚሆኑ ተግባራትን ከመፈጸማቸው ባሻገር በጾምና በጸሎት መጋደልን አልተዉም ነበር::
+ጊዜው ደርሶ በእግዚአብሔር ፈቃድ: በሕዝቡና ዻዻሳቱ ምርጫ: የእስክንድርያ 51ኛ ፓትርያርክ ሲሆኑ እርሳቸው እንደ ሌሎቹ አበው 'አልፈልግም' ብለው ነበር::
+ቀደም ሲል እንዳልነው አካላቸው በተጋድሎ የተቀጠቀጠ ነበርና በመንበራቸው ላይ ለብዙ ጊዜ መቆየት አልቻሉም::እግራቸውን በጠና በመታመማቸው ፈጣሪ ነፍሳቸውን እንዲቀበል ለመኑት: እርሱም ሰማቸው:: ሊቀ ዻዻሳት ሆነው በተሾሙ በ165ኛው ቀን (ማለትም በ5 ወር ከ15 ቀናቸው) በክብር ዐርፈው ተቀብረዋል::
††† ቸሩ አምላክ ከሰማዕቱ ጽናትን: ትእግስትን: ጸጋ በረከትን ይክፈለን::
††† ጥቅምት 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሐዲስ (ሰማዕት)
2.አባ ስምዖን ሊቀ ዻዻሳት
3.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ዘአርማንያ
4.ቅድስት ታኦድራ ልዕልት
5.ቅድስት ታኦፊላ
††† " ስለዚሕ ወንድሞቼ ሆይ ጣዖትን ከማምለክ ሽሹ:: ልባሞች እንደመሆናችሁ እላለሁ:: በምለው ነገር እናንተ ፍረዱ:: የምንባርከው የበረከት ጽዋ ከክርስቶስ ደም ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? የምንቆርሰውስ እንጀራ ከክርስቶስ ሥጋ ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን?... እኛ ብዙዎች ስንሆን አንድ ሥጋ ነን:: ሁላችን ያን አንዱን እንጀራ እንካፈላለንና:: "††† (1ቆሮ. 10:14-18)
††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
>>Click here to continue<<