TG Telegram Group Link
Channel: ከራድዮን
Back to Bottom
አንቺ ሴት
እንግዲህ ዘመነ አስተርዕዮም አይደል።
አስተርዕዮም መገለጥ ሲኾን በጽርዕ ቃል ኤፒፋንያ ይባላል። ይህንን የተዋሰው እንግልጣር ኤፒፋኒ (Epiphany)ይላል።
ከተገለጡ ምስጢራት አንዱ የወላዲተ አምላክ ክብርና አማላጅነት መኾኑ ይታወቃል።ከተርኈ ሰማይ ከምስጢረ ሥላሴ እና ከክርስቶስ የባሕርይ ልጅነት ቀጥሎ የሚነገረው ይህ ነው።

የወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት በገሃድ እንደተነገረው የድንግል ማርያምም የእግዚአብሔር እናትነት በገሃድ የተገነረበት ነውና።

አብ ይህ ልጄ ነው እንዳለ እግዚአ ኩሉ ክርስቶስ እናቱን አንቺ ሴት አላት። አብ አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእም ባሕርይ የምወልድህ ሳለው ልጄ አለው። ጌታም ሥጋሽ ከሥጋዬ አጥንትሽ ከአጥንቴ ሲላት ሴት ብሎ እናቱን ጠራት። ሴት እንዲህ ይተረጎማልና።ዘፍ ፪÷፳፫

ቀዳማዊ አዳም እናታችን ሔዋንን ሴት እንዳላት ዳግማዊው አዳም ክርስቶስ (፩ቆሮ ፲፭÷፵፭) እናቱን ሴት አላት ። ዘር ያልቀደመው ልደት ያለ እናት ከአባቱ እንደተወለደ ዘር ያልቀደመው ልደት ያለ አባት ከድንግል ማርያም መወለዱን ያገናዝባል።

ምስጋናውን ይቀበልልን🙏
-------------------------------
@gitim_menfesawi
“አንኳኩቼ አላገኘሁም” አትበል፡፡ ብቻ የለመንከው፣ ደጅ የጠናኸው አንተ የምትወደው ሳይሆን እግዚአብሔር የሚወድልህ ይሁን፡፡ ወደ እግዚአብሔር የተዘረጋ እጅ ፈጽሞ ባዶውን አይመለስም፡፡ ስለዚህ ራስህን፣ ልመናህን ምን ዓይነት እንደሆነ ፈትሽ እንጂ አንኳኩቼ አላገኘሁም አትበል፡፡ እንኳንስ ንጹሐ ባሕርይ የሆነው እግዚአብሔር ክፋት የሚስማማው ምድራዊ አባትም ለልጁ ጀሮውን አይደፍንም፡፡

አስቀድሞ ሕያዊት ነፍስን “እፍ” ብሎ እንዲሁ የሰጠን ጌታ፣ ኋላም ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው አንድ ልጁን ሳይራራ ከሰጠን እንደምን በዚህ ይታማል? እንደምንስ አይሰጠንም እንላለን? /ሮሜ.8፥32/፡፡ ልጁን የሰጠው እኮ ጭራሽ “ስጠን” ብለው ላልለመኑ አሕዛብም ጭምር ነው፡፡ ታድያ እንዲህ የምንለምን እኛማ እንዴት አብልጦ አይሰጠንም? የሚበልጠውን ሰጥቶን ሳለስ እንደምን ትንሹን አይሰጠንም እንላለን? ስለዚህ ከእኛ የሚጠበቀውን ሳናደርግ “እግዚአብሔር ጸሎቴን አይሰማም” የሚል የሰነፎች አባባል የምንናገር አንሁን፡፡ ጆሮን የፈጠረ ይሰማል!”

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ

(#ሰማዕትነት_አያምልጣችሁ
መጽሐፍ #በገብረ_እግዚአብሔር_ኪደ ገጽ 178)

----------
@gitim_menfesawi
#ጭንቀት - አባታዊ ምክር

እኛ ከእግዚአብሔር እድንርቅ ካደረጉን ነገሮች አንደኛው ጭንቀት ነው። ኦክስፎርድ ጭንቀት የሚለውን ሲተረጉመው "ከቁሣዊ ነገሮች ፍላጎት የሚመጣ ግፊት ወይም ውጥረት ይለዋል" የተሻለው ትርጉሙ ግን አላስፈላጊ ነገሮችን ከመፈለግ የተነሣ የአእምሮ ወይም የስሜት ድካም፣ ውጥረት ወይም ሕመም ማለት ነው። ጭንቀት ለሕይወታችን ከምንፈልጋቸው ወይም አላስፈላጊ ከሆኑ ነገሮች ፍላጎት የሚመጣ ግፊት ወይም ውጥረት ነው። ስለሆነም የጭንቀት መንስኤው ምንድን ነው? ስንል ተስፈኝነት ሆኖ እናገኝዋለን። በአጠገባችን ካሉ ሰዎች ቃል ከገቡልን፣ ከሚቀርቡን፣ ከቤተሰቦቻችን ወዘተ የምንጠብቀው አለ። ተስፈኝነት በሁለት መንገዶችሊመጣ ይችላል። ✞ስለ ሰወች ያለን ተስፈኝነት አለ። ሌላው ✞ሰዎች ስለ እኛ አላቸው ብለን የምናስበው ነው።

በማንኛውም መንገድ የተጨነቀ ሰው ከገጠማችሁ ከሁለቱ በአንዱ ምክንያት እነደሆነ ታረጋግጣላችሁ። ሌላ ሰው ለእኛ ዝቅተኛ ግምት ሠጥቶን ሊሆን ይችላል። ወይም እኛ ራሳችንን ዝቅ አድርገነው ሊሆን ይችላል። ወይም እግዚአብሔር እንደተወን አድርገን ልንወስድ እንችላለን። ወይም ከእግዚአብሔር እንደራቅን ሊሠማን ይችላል።

ጭንቀት ከእነዚህ የአንዱ ስሜት ውጤት ነው።
የቁስ እቃ ፍላጎት እንድንጨነቅ ያደርጋል። ምን ማድረግ እንዳለብን አናውቅም አንዳንድ ጊዜ አወንታዊ በሆነ መልኩ ለስሜቱ ምላሽ እንሰጣለን። አንዳንድ ጊዜ ደግሞ አሉታዊ መልስ እንሰጣለን። ሌላ ጊዜ ደግሞ አወንታዊም አሉታዊም ሳይሆን ይቀራል።

ከጭንቀት ለመላቀቅ የሚረዳ ዋነኛው ዘዴ ቤተ ተፈጥሮአዊ ማንነታችንን ማሰብ ነው። ቁሣዊ ሆነን አልተፈጠርንም። የተፈጠርነው በእግዚአብሔር አርአያ እና አምሳል ነው። መቅደሱ ሆነን ነው የተፈጠርነው። ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር ነው የተፈጠርነው። ግፊቱም፣ ጭንቀቱም፣ ሕመሙና፣ ውጥረቱ፣ በመጣ ጊዜ ለእግዚአብሔር አሳልፈን መስጠት ይኖርብናል። ከእግዚአብሔር ኃይል በላይ የሆነ ግፊት ወይም ውጥረት የለም። ስለሆነም እኔ ተሸክሜ ከምጨነቅ እግዚአብሔር እኔን ሆኖ እንዲሸከም አደርጋለሁ። እርሱ ጫናወቻችንን ያቀላል።

ዮሴፍ በብዙ ጫናወች ውሰጥ ይኖር ነበር። ወድሞቹ ጉድጓድ ላይ ሲጥሉት ምናልባት መረዳት በማይችልበት በሕፃንነቱ ጊዜ ነበረ። እንደገናም ለባርነት ሸጡት። ከቤተሰቡም ጋር ተለይቶ መኖር ጀመረ። የንጉሱ የፈርኦን ሚስት በሐሰት ከሰሰችው። በዚህም የተነሳ እስር ቤት ተጣለ። በእስር ቤት እያለ ማንም የሚያስታውሰው አልነበረም። ይህ እንግዲህ መጠነ ሰፊ ወደ ሆነ ጫና ውስጥ ያመጣዋል። ሆኖም ግን ዮሴፍ እንዴት ለመፍታት ሞከረ? ችግሩን እንዴት ተቋቋመው? በእያንዳንዱ ሁኔታ ዮሴፍ ራሱ ዮሴፍ ነበረ። አልተለወጠም። በሁሉም ሁኔታዎች ተመሣሣይ ማንነት፣ ፍቅር፣ እምነት፣ ነበረው። እግዚአብሔርን አዘውትሮ ይጠራ እና ይለምን ነበረ። እግዚአብሔርም ሁል ጊዜ አጠገቡ ነበረ።

አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ
____________
@gitim_menfesawi
አንድ ሰው መጥቶ ለአንድ ቅዱስ አባት ጥያቄ አቀረበለት "ተአምር መሥራት እፈልጋለሁ፣ እንዴት ላድርግ?" ቅዱሱ አባት መለሰለት፦
"አንድን ሰው ወንጌል እንዲያነብ ካስተማርከው ዓይን አበራህ ማለት ነው፤ ድሆችን እንዲረዳ ካስተማርከው ሽባውን አዳንክ ማለት ነው፤ ወደ ቤተ ክርስቲያን መሔድ እንዲችል ካደረግህ አንካሳውን ፈውሰሃል፤ ሙት ማንሣት ከፈለግህ ደግሞ ንስሓ እንዲገባ አድርገው ያኔ የሞተ ሰውን አስነሥተሃል ማለት ነው። በል ሒድና ተአምር ሥራ!"
------------------
@gitim_menfesawi
❖ ሌሎች በድንግልና የኖሩ ሴቶች "ለሞት የሚሆኑ ልጆችን አንሰጥህም"በማለት ሞትን ተቃወሙት። ድንግል ማርያም ግን አንድ ልጅ በመውለድ በልጅዋ ሞት እራሱ እንዲሞት አደረገችው። ከዐለት ጋር እንደተጋጨ የተፈረካከሰው በማሕፀንዋ ፍሬ ነውና ሞት ወደ እርስዋ ሲቀርብ ተብረከረከ።
ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ
🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸
@gitim_menfesawi
ተወዳጆች ሆይ! ሌላ ሰው አደረሰብኝ የምትሉት ጉዳት ምንድነው? ተቆጥቶ ሰደበኝ፤ ያለ ስሜም የሆነ ስም ሰጠኝ የሚል ነውን? ታዲያ ይኼ ምን ጉዳት አለው? በፍጹም ጉዳት የለውም፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ነገሮች ጉዳቶች ሳይሆኑ ትዕግሥተኞች ከሆናችሁ ጥቅማቸው የበዛ ነውና፡፡ ሲጀምር በእናንተ ላይ ጉዳት ለማድረስ የሚፈልገው ሰው የሚያደርገውን አያውቅም፡፡ የሚያደርገው ሁሉ ወዶና ፈቅዶ አይደለም፡፡ምንም እንኳን እናንተን የጐዳ ቢመስለውም ራሱን እየጐዳ ነው፡፡ የብዙዎቻችን ችግር ጐጂውና ተጐጂው ማን መሆኑን ለይተን አለማወቃችን ነው፡፡ ምክንያቱም ይኼንን ለይተን ብናውቅ ኖሮ ራሳችንን ለመጉዳት ባልተነሣሳን ነበር፤ ሌሎች ክፉ ይደርስባቸው ዘንድ ባልጸለይን ነበር፤ ማንንም መጕዳት እንደማንችል በገባን ነበር፡፡ ትልቁ በደል ደግሞ ክፉን መቀበል ሳይሆን በሌሎች ላይ ክፉትን መፈጸም ነው፡፡

ስለዚህ ከዛሬ ጀምራችሁ ሌላ ሰውን በድላችሁ ከሆነ ራሳችሁን ውቀሱ፤ ሌላው ክፉ አድርጐባችሁ እንደሆነ ግን ለእናንተ ያደረገው ነገር መልካም ነውና ጸልዩለት፡፡ ምንም እንኳን ሰውዬው እናንተን ለመጥቀም ብሎ ያደረገው ባይሆንም በመታገሣችሁ ግን ትልቅ ጥቅምን ታገኛላችሁ፡፡ ክፉ አደረገብኝ የምትሉት ሰውዬ ድርጊቱ ክፉ እንደሆነ ሰዎችም የእግዚአብሔር ቃልም ይፈርዱበታል፤ እናንተ ግን እንዲህ ስትታገሡ ለጊዜው ምንም የተጐዳችሁ ቢመስላችሁም ጌታ እንደተናገረ ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነው።

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸
@gitim_menfesawi
ከንቱ ውዳሴ

አንዳንድ ጊዜ ለእኛ ጥሩ የመሰለንን ነገር ልናደርግ እንችላለን። ለምሳሌ
ሁለት ሰዎችን አስታርቄ ሊሆን ይችላል። ከዚያ በኋላ ግን ለእነሱ የተናገርኳቸውን ጥበብ የተሞሉ ንግግሮች ማስታወስ እጀምራለሁ።በውስጤም "ቀላል ሰው አይደለሁም ለካ!" እላለሁ። አንድ የሰንበት ትምህርት ቤት መምህር የማስተማር ጸጋ ሊሰጠው ይችላል። ይህ ጸጋ ግን የተሰጠው ከመምህሩ ብቃት ሳይሆን ለተማሪዎቹ ሲባል ነው። ነገር ግን እሱ የተናገራቸውን ቃላት እያስታወሰ ከእግዚአብሔር የተሰጡ መሆናቸው ቀርቶ ከራሱ ያመነጫቸው አድርጎ በማሰብ ራስን ከፍ ወደ ማድረግ ልቡ ይሞላል።

ይህንን ፈተና እንዴት እንደምትዋጋው መንገዱን ልንገርህ! እንዲህ ዐይነቱ አሳብ በኅሊናህ ማደግ ሲጀምር ነቢዩ በለዓምን ለመገሠጽ እግዚአብሔር አህያን እንደተጠቀመ አስታውስ!(ዘኁ.፳፪÷፳፩_፵፫)
ለራስህም እንዲህ በለው፦"በተናገርኳቸው ቃላት እንድመካ ከበለዓም አህያ የተሻለ ሥልጣን የለኝም!"
✤✤✤✤✤✤✤✤
@gitim_menfesawi
ኪዳነምሕረት
🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸
+ የእርሷ ኪዳን የ6ቱን አበው ኪዳናት ፍፁም በማድረጉ "የኪዳናት ማሕተም" ይባላል።
የድንግል ማርያም ኪዳኗ ከሲዖልና ከገሃነም ሊታደገን አቅሙ አለውና።
መድሃኒታችን ክርስቶስ ለድንግል እናቱ ቃልኪዳኑን ያፀናላት ደግሞ ካረገ ከአመታት በኋላ ጐልጐታ ላይ ነው።
+ እመብርሀን በዚያ ቆማ ስለ ኃጥኣን ስታለቅስ "እናቴ ሆይ! በስምሽ ያመነውን በቃልኪዳንሽ የተማፀነውን እምርልሻለሁ" ብሎ ቃልኪዳን ገብቶላታል
ዛሬም እኛ ኃጥኣን ልጆቿ ከእሳት እንደምታስምር አምነን በጥላዋ ስር እንኖራለን።

+ ኢትዝክሪ ብነ አበሳነ፡ኃጥያተነ፡ወጌጋየነ። ማርያም እሙ ለእግዚእነ። በኪዳንኪ፡ወበስደትኪ ድንግል ተማሕፀነ።
🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸🌸
@gitim_menfesawi
ኪዳነ ምህረት

#16

@gitim_menfesawi
የጦርነት ድልን ቤተክርስቲያን ለምን ታከብራለች?
[#አድዋ]

በሐዘን ማቅ ውስጥ ገብታ የምትዳክረው ኢትዮጵያ በርከት ባሉ የትርክትና የፍላጎት ግጭቶች የተሞላውን የአድዋ ድል በዓልን እያከበረች ነው። በአሉ ለኢትዮጵያ ወሳኝ ታሪካዊና ማህበረ ፖለቲካዊ በአል ቢሆንም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንም በራሷ ሥርዓትና ቀኖና ታቦት አውጥታ ንግስ አንግሳ ታከብረዋለች።

ይህን ማክበሯ መፍቀሬ ሚኒሊክ፣ የነፍጠኞች ዋሻ ፣ ሰሜናዊት እያስባለ በብዙዎች ቢያስተቻትም ዝክረ አድዋን ሳታቋርጥ ቀጥላለች።ለመሆኑ በሁለት ሐገራት መካከል የተደረገን የጦርነት ድል መንፈሳዊት ቤተክርስቲያን ማክበር አለባት?

በቅድስት ቤተክርስቲያን በዓላት የሚከበሩት ከዚህ በታች ባሉ ምክንያቶች ነው።
1. በነገረ ድህነት ወሳኝ ምዕራፍ የተጫወቱ ቀናት /በአብዛኛው የሐዲስ ኪዳን በዓላት እለተ እሁድን ጨምሮ
2. ጠብቆተ እግዚአብሔር የታየባቸው ቀናት /አብዛኛዎቹ ብሉይ ኪዳን ጠቀስ በዓላት ቀዳሚት ሰንበትን ጨምሮ
3. የእግዚአብሔር ቅዱሳን የተወለዱበትና /ወይም ያረፉበት ቀናት
4. እግዘብሔር በቅዱሳኑ ድንቅ ያደረገባቸው ቀናት /ስባረ አፅሙ ለቅዱስ ገዮርጊስ ፣ የህዳር ፅዮን የመላእክት በዓላት .....
5. በአለማቀፋዊቷም ሆነ በሀገራዊቷ ቤተክርስቲያን ወሳኝ የታሪክ ምዕራፍ ያረፈባቸው ቀናት /ጰራቅሊጦስ፣ የኒቂያ ቆስጠንጢንያና ኤፌሶን የአለም አቀፍ ጉባኤያት፣ የአርመን ቤተክርስቲያን ጭፍጨፋ፣ የኮብቲክ ቀን፣ በዓለ ሲመቱ ለፓትርያርክ....

እነዚህ በዓላት እንደየክብራቸውና ድርሻቸው መጠን በመላው አለም ወይም በአንድ ሐገር አልያም በአንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያን በተለያዩ ስርዓቶች ይከበራሉ።

የአድዋ ድል በዓልን ቤተክርስቲያን ስታከብርም ከነዚህ ከላይ ከተጠቀሱት ውስጥ አብዛኛውን ስለሚያሟላ ነው።

የአድዋ በዓል እንደ ጠብቆተ እግዚአብሔር ማሳያ።

እግዚአብሔር የኢትዮጵያም የጣሊያንም አምላክ ነው። ማንንም ለይቶ አይደግፍም ነገር ግን በድንግል ማርያም ፀሎት እንደምናገኘው ብርቱዎችን ያዋርዳል የተዋረዱትንም ከፍ ከፍ ያደርጋል። በመሆኑም ብርቱ ነኝ ብሎ ምንም ጠብን ባልሻተች ሀገር ላይ የተከፈተን ጦርነት በምንም መልኩ ሚደግፍ አምላክ አይደለም። በመሆኑም ሳይበደል ለመበደል ዘመናዊ ጦርን ታጥቆ የመጣን ሰራዊት ለደካሞችና በአብዛኛው የቤት ቁሳቁስና የግብርና መሳሪያዎችን እንዲሁም አነስተኛ ጦር በታጠቁ ኢትዮጵያዊያን ገበሬዎች እጅ ጥሎታልና ይህ ዕለት የእግዚአብሔር ቀን ነው።

የአድዋ ድል እንደ ቅዱሳን ተራዳኢነት ማሳያ

የአድዋ በአል ከቅድስት ድንግል ማርያምና ከሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ተራዳኢነት ጋር የበዛ ቁርኝት አለው። በተለይም እነዚህ ቅዱሳን ለተገፉ ደራሽ ከመሆናቸው ባሻገር በኢትዮጵያ የአሥራትነት ና ገበዝነት ሚና እነደሚራዷቸው ያመኑ ኦርቶዶክሳውያን ኢትዮጵያውያን ታቦታቱን አሰልፈው ምህላ እያስደረሱ በተራሮች መሐል ተዋድቀዋል። ሞተዋል ቆስለዋል ደምተዋል። ከጎናቸው የቅድስት ድንግል ማርያም ረዳትነት የቅዱስ ጊዮርጊስ ጥበቃ አልራቀም ነበር። ፈረንጆቹ እኛን የሚመስል በእነሱ ፈረስ ላይ ተቀምጦ ይወጋን ነበር እስኪሉ ድረስ ጥበቃው በጠላት ወገን ጭምር የተገለጠ ነበር።

አድዋ እንደ ወሳኝ የቤተክርስቲያን የታሪክ ክፍል

የአድዋ ጦርነት ኬልቄዶናዊ ሀሳብ ተሸርቦባት የነበረች ቤተክርስቲያንን የታደገ ድል ነው። ለበርካታ ዘመናት ከምዕራቡ የአውሮፓ አለም የመጡ ጦሮች አላማቸው ኢትዮጵያን መቀራመት ብቻ ሳይሆን ቤተክርስቲያንን ካቶሊክ ማድረግ ቢሆንም የሮም መንበር በነበረባት የጣሊያን ሁለት ወረራዎች ግን በግልጽ አንዲት ቤተክርስቲያን በሌላ ቤተክርስቲያን ላይ የጦር ወረራ ያወጀችበትና መሳሪያ ባርካ ሁሩ ወኢትመሀሩ ያለችበት ወረራ ግን እጅጉን ያፈጠጠ ነበር። ትናንት በሱሲኒዮስ በርካቶችን ለሰማያዊ ርስት የተገቡ ያደረገችው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን መሳሪያ ከመባረክ አልፋ በጦርነቱ ውስጥ አገልጋዮቿን ትጥቅ አስለብሳ እንዲሁም ለቤተክርስቲያን አባቶች መደለያ በመስጠት በሌሎች የአፍሪካ ሐገራት ያደረገችውን የታጣቂዎች የወንጌል ተልዕኮ ለማስፈፀም አቅዳ የነበረ ቢሆንም አስቀድሞ በአድዋ ድል ኋላም በአምስት አመቱ ጦርነት እንዲጨነግፍ ሆኗል።

እነዚህን ምክንያቶች ማዳመጥ የማይችሉ ምንም እንኳን ስም ቢያወጡላትም ቤተክርስቲያን ግን በዓሉን ማክበሯን የምታስታጉል አይደለችም ያዳናትን ታውቃለችና።

@gitim_menfesawi
የሚፈውስ እንባ
/በቅዱስ ኤፍሬም /

ሰውን የምታድን ክርስቶስ ሆይ! ከአንተ በቀር ማን ያድነኛል? የድኅነት ምንጭ ከኾንከው ከአንተ በቀር የታመመችውን ነፍሴን ማን ይፈውሳታል? አቤቱ ሆይ! እንኪያስ የታመመችውን ችግረኛ ሴት እንደፈወስካት እኔንም ከጥፋት ከምረረ ገሃነም አድነኝ፡፡ ምሕረት ቸርነትኅ በእኔ ላይ ትኹን፡፡ ጠላቴን ድል አደርገው ዘንድ እርዳኝ፡፡ ብርቱ በምትኾን ክንድህ ደካማ የምኾን እኔን አበርታኝ፡፡ አበርታኝና ለተጋድሎ የተዘጋጀኹ እንደኾንኩ ዐይቶ ጠላቴ ይራድ፤ ይንቀጥቀጥ፤ ይፈርም፡፡ አበርታኝና ጠላቴ የተዋረደ ይኹን፡፡ አበርታኝና ጠላቴ (ዲያብሎስ) በሐፍረት ከፊቴ ይመለስ፡፡ አበርታኝና እኔም ስምኽን ከፍ ከፍ ላድርገው፡፡

አቤቱ ሆይ! ጐስቋላ የምኾን እንባዬን ተቀበልልኝ፤ ዕዳዬንም ፋቅልኝ፡፡ ፍቅርኅ የእኔን የበደለኛውን የክፉ ምግባሬ ፍሬ ይደምስስልኝ፤ ምረረ ገሃነምም አያግኘኝ፡፡ ቸርና ሰው ወዳጅ ሆይ! ዕዳዬን ደምስስልኝና ጠላቴ ይፈር፡፡ ፈተናውን ድል አደርግ ዘንድ፥ ድል አድርጌም ዘወትር ከአንተ ጋር እኖር ዘንድ ምሕረት ቸርነትህ ከእኔ ጋር ትኹን፡፡

አቤቱ ሆይ! አልቅሳ ሰምታኻታልና፥ በሚፈውስ እንባ አጥበኻታልና፥ ፍጥረትን ኹሉ ለፈጠርከው ለአንተም ቤተ መቅደስህ አድርገኻታልና በደለኛ የምትኾን ሰውነቴ፥ ከባሕርይ አባትህ ከአብ ከባሕርይ ሕይወትህ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ታከብርኻለች፡፡ አሜን!!!

#ገብረ_እግዚአብሔር_ኪደ
           
@gitim_menfesawi
ደብረዘይት በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

የተወደደ አባት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ ደብረዘይት በተናገረበት ድርሳን እንዲህ አለ፦

"የክርስቶስ ተቃዋሚ እንዴት እንደሚመጣ ከነገራቸው በኋላ እርሱ (ጌታ) ራሱም እንዴት እንደሚመጣ እንዲህ ሲል ነገራቸው፡- “መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ፥ የሰው ልጅ መምጣት እንዲሁ ይኾናልና፡፡”

መብረቅ አለ! ስለ መብረቅ ብልጭታ ማንም እንዲመሰክር አይፈለግም፡፡ በእልፍኝ ለተቀመጡም፣ በቤት ውስጥ ላሉም፣ በአጠቃላይ በዓለም ኹሉ ላሉት በቅጽበት ይታያልና፡፡ ክርስቶስ ክብሩን እየገለጠ እንዲህ ድንገት ይመጣል፡፡ ሌላ ምልክትም አለው፡፡ በድን ወዳለበት በዚያ አሞራዎች እንዲሰበሰቡ ክርስቶስ ሲመጣም አእላፍ መላእክት፣ ቅዱሳን ሰማዕታት፣ ቅዱሳን ሐዋርያት፣ ቅዱሳን ነቢያት፣ ጻድቃን ኹሉም ይሰበሰባሉ።

ከዚያ በኋላ በጣም አስፈሪ ድንቅ ይፈጸማል፡፡ በክርስቶስ ተቃዋሚ፣ በሐሰተኞች ነቢያት የሚደረገው የማታለል ሥራ ካለቀ በኋላ፣ ብዙዎች ሃይማኖታቸውን ከለወጡ በኋላ ወዲያው ተፈጥሮ መልኳን ትለውጣለች፤ ፀሐይ ይጨልማለች፤ ጨረቃም ብርሃንዋን አትሰጥም፥ ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፡፡ በዚያ ቅጽበት በጨለመው ዓለም ፋንታ የክርስቶስ ብርሃነ መለኮት ይተካል፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ሌሊት የለም፡፡ ከዋክብት በተፈጠሩ ጊዜ መላእክት በታላቅ ድምጽ እግዚአብሔርን እንዳመሰገኑ (ኢዮብ.38፡7) የዚያን ጊዜም ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ በጠፈር ሠልጥነው የነበሩ ፀሐይ ስትጨልም፣ ጨረቃ ብርሃኗን ስትከለክል፣ ከዋክብት ሲወድቁ አይተው የሰማያት ኃይላት (መላእክት) ይናወጣሉ፤ ይደነቃሉ።

በዚያን ጊዜም የወልደ እጓለ እመ ሕያው ክርስቶስ ምልክቱ፣ አሠረ ቅንዋቱ በሰማይ ይታያል፡፡ በሌላ አገላለጽ መስቀሉ ከፀሐይ ብርሃን ይልቅ ደምቆ ይታያል፡፡ ዳግመኛ ላትታይ ፀሐይ ጨልማለችና ብርሃነ መስቀሉ ይንቦገቦጋል፡፡ ከእናንተ መካከል “ስለ ምን መስቀሉ በዚያ ሰዓት ይታያል?” ቢል ጌታ የሰቀሉትን አይሁድ ይወቅስ ዘንድ ነው ብለን እንመልስለታለን፡፡

ከዚህ በኋላ ንጉሡ በፍርድ ወንበሩ ይቀመጣል፡፡ የቆሰለውን ቁስል ብቻ ሳይኾን የሞት ተግሣጽንም እያሳየ መጥቶ ይቀመጣል፡፡ በዚያን ጊዜም የምድር ወገኖች የሚያምኑበት ሰዓት አይደለምና በወልደ እግዚአብሔር ባለማመናቸው ኹሉ ዋይ ዋይ ይላሉ፡፡ ሊያከብሩትና ሊታመኑት ሲገባ ሲሳለቁበት ኑረዋልና ላይጠቅማቸው ዋይ ዋይ ብለው ያዝናሉ፡፡ የምድር ወገኖች የራሳቸውን ኃጢአት እያነበቡ ዋይ ዋይ እያሉ ያለቅሳሉ፡፡ በመዋእለ ሥጋዌው ወደ ኢየሩሳሌም በአህያ ላይ ተጭኖ ሲገባ በጌታ ስም የሚመጣ ብሩክ ነው እንዳላሉ አሁን ግን ዋይ ዋይ ይላሉ፡፡

የሰው ልጅንም በኃይልና በብዙ ክብር በሰማይ ደመና ሲመጣ ያዩታል፤ መላእክቱንም ከታላቅ የአዋጅ መለከት ድምፅ ጋር ይልካቸዋል፡፡ ከሰማያትም ዳርቻ እስከ ዳርቻው ከአራቱ ነፋሳት ለእርሱ የተመረጡትን ሙታን ይሰበስባሉ።

"ወዮ! በዚያች አስፈሪ ቀን ለእኔ ወዮታ አለብኝ! የመለከቱን ድምጽ ስሰማ መደሰት ሲገባኝ ስቃይ ይሰማኛልና ወዮታ አለብኝ፡፡ ስለዚያች ቀን ሳስብ ውስጤ በረዓድ ይመላል፤ አምርሬ አለቅሳለሁ፤ በውስጤም እቃትታለሁ፡፡ 'ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን' ከሚላቸው ከጻድቃን ጋር የሚያስደምር መልካም ሥራ የለኝምና፤ እንደ አምስቱ ሰፎች ቆነጃጅት፣ መክሊቱን እንደቀበረ ታካች ባርያም ኾኛለሁና አለቅሳለሁ፤ ፊቴ በእንባ ይታጠባል፡፡ የማጣውን ክብር፣ የሚቀርብኝን የድል አክሊል፣ ለጊዜው ሳይኾን ለዘለዓለም እንደማጣው ሳስብ አነባለሁ፡፡

ልጆቼ! ይህን የሚሰማን እኔ ብቻ እኾን ወይስ እናንተም ይሰማችኋል? ከማን ወገን ናችሁ? ደስ ከሚላቸው ወይስ ላይጠቅማቸው ዋይ ዋይ ከሚሉቱ ወገን?"

(በገብረ እግዚአብሔር ኪደ)
@gitim_menfesawi
አንድ ሰው መፍትሔ የሌለው የሚመስል መከራ ሊገጥመው ይችላል። በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር ድምፅ መከራው የገጠመው ጥቂት ኃጢአቶችን ስለ ፈጸመ መሆኑን ከማስጠንቀቂያ ጋር ይነግረዋል። አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ቃሉ ንስሓ ከገባህ መከራው ፍጻሜ ያገኛል እያለ ውስጡን ሲመክረው ይሰማል። ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር ስለ ንስሓው ሲል ለሰውየው ይራራለታል።

የእግዚአብሔር ድምፅ አንድ ሰው ሲታመም ወይም እርሱ የሚወደው ሌላ ሰው ሲታመም ሊመጣ ይችላል። በዚህ ጊዜ እንዲጸልይ ወይም ስእለት እንዲሳል የሚመክረውን ድምፅ ከውስጡ ይሰማል ይህ ድምፅ የእግዚአብሔር ድምፅ ነው።

የዮሴፍ ወድሞች እህል ሊገዙ ወደ ግብጽ ከወረዱ በኋላ በዚያ ችግር ሲገጥማቸው እርስ በእርሳቸው እንዲህ በማለት ተነጋግረው ነበር፦ "በእውነት ወድማችንን በድለናል እኛን በማማጠን ነፍሱ ስትጨነቅ አይተን አልሰማነውና ስለዚህ ይህ መከራ መጣብን።"/ዘፍ 42፥21/ ከዚህ በኋላ ለዮሴፍ እንዲህ ብለውታል፦ "ለጌታዬ ምን እንመልሳለን? ምንስ እንናገራለን? ወይስ በምን እንነጻለን? እግዚአብሔር የባሪያዎችህን ኃጢአት ገለጠ"/ዘፍ 44፥16/ ኃጢአታቸውን እንዲያስታውሱ ኋላም እንዲገሰጹ ያደረጋቸው የእግዚአብሔር ድምፅ ነው።

ነቢዩ ዳዊት የጌራ ልጅ በሆነው በሳሚ ሲሰደብ የእግዚአብሔር ድምፅ ውስጡ ስላለፈ ኃጢአቱ እየወቀሰው መሆኑን አዳምጧል። ስለሆነም በዙሪያው ለነበሩ ሰዎች "እግዚአብሔር ዳዊትን ስደበው ብሎታልና ይርገመኝ።" /2ኛ ሳሙ.16፥10/ በማለት በግልጽ ተናግሯል።

ረሀብና የመሬት መንቀጥቀጥ በዓለም ሲደርስ የእግዚአብሔር ድምፅ በመላው ዓለም ውስጥ ይሰማል። በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር ድምፅ የሚናገረን "ወደ እኔ ተመለሱ እኔም ወደ እናንተ እመለሳለሁ።" /ሚል 3፥7/ እያለ ነው። ይህ ድምፅ በረሀቡ ወይም በመሬት መንቀጥቀጡ ጉዳት ለደረሰባቸው ሀገሮች የሚሆን የእርዳታ ጥሪ ለማሰማት ወይም ሌሎቹ ከእነርሱ ትምህርት በመውሰድ ንስሓ እንዲገቡ ለማድረግ ወይም ከእግዚአብሔር ጋር ለመገናኝት ዝግጅት እንዲያደርጉ ነው።

ስለዚህ ማንኛውም ዓይነት መከራ ውስጥ ስትገቡ ከውስጣችሁ ያለውን የእግዚአብሔር ድምፅ አድምጡት እርሱ ለእናንተ ሊነግራችሁ የሚወደው ምን እንደ ሆነ ታውቃላችሁና።

#አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ

@gitim_menfesawi
" እንኳን ለጾመ ነቢያት በሰላም እና በጤና አደረሳችሁ"

ይህ ፆም ከቤተ ክርስቲያናችን የአዋጅ ፆሞች ውስጥ አንዱ ሲሆን አበው ነብያት የጌታችን የመድሃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መውረድ መወለድ በትንቢት መነፅር እየተመለከቱ የፆሙት ታላቅ ፆም ነው።

ዛሬም እኛ ክርስቲያኖች የአባቶቻችንን ፈለግ ተከትለን በፆምና በፀሎት ወቅቱን በማሳለፍ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ዝቅ አድርጎ ወደ አለም መምጣቱንና የዓለም ቤዛ መሆኑን የምናስብበት ነው።

ይህንን ጾም በዘመነ ብሉይና በዘመነ ሐዲስ ብዙ ቅዱሳን ጾመውታል፤ በዚህም ምክንያት የሚከተሉት ስያሜዎች አሉት፡፡ እነርሱም፤

፩. ጾመ አዳም:- አዳም ዕፀ በለስን በልቶ ከገት ከተባረረ በኋላ; በፈጸመው በደል አዝኖ ፥ ተክዞ፤ አለቀሰ (እንባ ቢያልቅበት እዥ እስከሚያፈስ፤ እዥ ቢያልቅበት ደም በዓይኑ እስከሚፈስና ዓይኑ ይቡስ ወይም ደረቅ እስከሚሆን ድረስ አለቀሰ) ፥ ጾመ፣ ጸለየ፡፡ ከልብ የሆነ ጸጸቱን፣ ዕንባውን፣ በራሱ መፍረዱንም እግዚአብሔር አይቶ ተስፋ ድኅነት ሰጠው፡፡ ‹‹ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ፣ በደጅህ ድኼ፣ በዕፀ መስቀል ተሰቅዬ፣ ሞቼ አድንሃለሁ፡፡›› የሚል ነው፡፡ /ገላ. ፬፥፬፣ መጽ.ቀሌምንጦስ/ ስለዚህ ጾሙ የተሰጠው ተስፋ ፥ የተቆጠረው ሱባኤ ስለተፈጸመበት ‹‹ጾመ አዳም›› ይባላል፡፡

፪. ጾመ ነቢያት:- ነቢያትም የምሥጢረ ሥጋዌ ነገር ተገለጦ ስለታያቸው፣ ክርስቶስ ለሰው ልጅ የሚከፍለውን የፍቅር ዋጋ በትንቢት ተመልክተው ጾመውታልና ጾመ ነቢያት ይባላል፡፡ ይህ ጾም ከአባታችን አዳም እስከ መጥምቁ ዮሐንስ ድረስ የተነሱ አበውና እናቶች: ድኅነትንና ረድኤትን ሲሹ የጾሙት ጾም ነው:: በተለይ አባታችን አዳም: ቅዱስ ሙሴ: ቅዱስ ኤልያስ፣ ቅዱስ ዳንኤል ና ቅዱስ ዳዊት በጾማቸው የተመሰከረላቸው ቅዱሳን ናቸው:: (ዘዳ 9:19, ነገ. 19:8, ዳን. 9:3፣ መዝ. 68:10, 108:24) ቅዱሳን ነቢያት በጭንቅ በመከራ ሆነው የጾሙት ጾም ወደ መንበረ ጸባኦት ደርሶ: ወልድን ከዙፋኑ ስቦታል:: ለሞትም አብቅቶታል::

፫. ጾመ ሐዋርያት:- ሐዋርያት ‹‹ትንሣኤን ዐቢይ ጾምን ጾመን እናከብራለን፣ ልደትን ምን ሥራ ሠርተን እናከብረዋለን?›› ብለው ከልደተ ክርስቶስ በፊት ያሉትን ፵፫ ዕለታት ጾመዋልና፡፡

፬. ጾመ ማርያም:- እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር አምላክ ቅድስናዋን አይቶ በቅዱስ ገብርኤል ብሥራት ወልደ አምላክን ያለ ሰስሎተ ድንግልና በግብረ መንፈስ ቅዱስ ጸንሳ እንደምትወልደው ቢነግራትም የትሕትና እናት ናትና ‹‹ምን ሠርቼ የሰማይና ምድርን ፈጣሪ እችለዋለሁ?›› ብላ ጌታን ከመውለዷ አስቀድማ ጾማለችና ‹‹ጾመ ማርያም›› ይባላል፡፡

፭. ጾመ ፊልጶስ:- ሐዋርያው ፊልጶስ በአረማውያን ዘንድ ገብቶ እያስተማረ ሳለ በሰማዕትነት ሲሞት፤ አስክሬኑ ከደቀመዛሙርቱ ስለተሰወረ፤ እግዚአብሔር የተሰወረውን የመምህራቸውን አስክሬን እንዲገለጽላቸው ከኅዳር ፲፮ ጀምረው ጾመው በሦስተኛው ቀን የመምህራቸው አስክሬን ተመልሶላቸዋል፤ ነገር ግን አስከሬኑ ቢመለስላቸውም ጾሙን ግን እስከ ልደት ቀጥለዋል፡፡

፮. ጾመ ስብከት:- የወልደ እግዚአብሔርን ሰው መሆን ያስተማሩበት፥ የሰው ልጆች ተስፋ የተመሰከረበት፥ የምስራች የተነገረበት ስለሆነ ጾመ ስብከትም ይባላል፡፡

፯. ጾመ ልደት:-
የጾሙ መጨረሻ (መፍቻ) በዓለ ልደት ስለሆነ ‹‹ጾመ ልደት›› ይባላል፡፡

ጾምን ትእዛዝ ስለሆነ ብቻ ሳይሆን የፍቅርና የበረከት ምንጭ በመሆኑ ጭምር ደስ እያለን ብንጾመው የቅዱሳኑ በረከት ያድርብናል፡፡

( ፆመ ነብያት ወይም የገና ፆም ማክሰኞ ህዳር 15 ይጀምራል. ታህሳስ 29 በዕለተ ሐሙስ ይፈታል። ይህ ማለት የዘንድሮ የገና ፆም ቅበላ እስከ ሰኞ ነው ከማክሰኞ ጀምሮ የፍስክ ምግቦች አይበሉም። )

https://hottg.com/gitim_menfesawi
" ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ "
ማቴ 26:41
ልዩ ሦስት የምትሆን አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ሆይ እስከ መጨረሻይቱ ሕቅታም ድረስ ልዩ ሦስትነትህን ማመንን ፈጽምልን !
ምሳሌ 3:5
ትንቢተ ናሆም 1:7
መዝሙረ ዳዊት 47:6
መዝ 119:103
HTML Embed Code:
2024/04/18 07:05:05
Back to Top