TG Telegram Group Link
Channel: ወግ ብቻ
Back to Bottom
"ሴቶች በምንም አይማልሉም አትድከሙ!"
(አሌክስ አብርሃም)

በነገራችን ላይ እንደምታስቡት ሴት"መጀንጀን" ላይ አሪፍ አይደለሁም! ስለመጨረሻ ጅንጀናየ ላውጋችሁ! የሆነ ጊዜ አምስት መንገዶች አስር ማሳለጫዎች ምናምን የሚል የሬዲዮ ፕሮግራም ላይ ሴት ልጅ በራሱ የሚተማመን ወንዳወንድ ወንድ ትወዳለች የሚል ነገር ሰማሁ! እና አንዲት በዛ ሰሞን የወደድኳትን ልጅ ማማለል ፈለኩ! ተቀጣጥረን ተገናኘን ምሳ አብረን በላን (በድሮሮሮሮሮሮሮ ጊዜ የዛሬ ስድስት ዓመት ሰዎች ምሳ ይገባበዙ ነበር) እና ከመሬት ተነስቸ ጀብዱ ነገር ማውራት ጀመርኩ!

"ይገርምሻል የሆነ ጊዜ አንድ ዳይኖሰር የሚያክል በሬ ከቄራ አመለጠ ፤ እና ከቄራ ቡልጋሪያ ድረስ ሰባት ወንዶች ሶስት ሴቶች ሁለት መኪና በቀንዱ እየወጋ አተረማመሰው! ፖሊስ ሁሉ ማስቆም አልቻለም! እና እኔ ስደርስ ወደሆኑ አሮጊት ቀንዱን አሹሎ እየሮጠ ነበር ... በባልቴቷና በበሬው መካከል ሶስት የበሬ እርምጃ ሲቀር ተፈትልኬ ሮጥኩና መሀላቸው ገብቸ ስቆም ጫማየ እንደመኪና ጎማ ፉጭጭጭጭጭጭ አለ! በሬው ደንግጦ ቆመና ተፋጠን እንደቆምን በቀስታ ቀረብኩት .... በእግሩ አስፋልቱን እየቆፈረ ሊወጋኝ ሲሞክር ሸወድኩትና አንገቱ ላይ የታሰረውን ገመድ ቀጨም አድርጌ ለባለቤቱ አስረከብኩ! ይገርምሻል በተፈጥሮየ አልፈራም!

ልጅቱ ስትሰማኝ ቆየችና የበሬውን ነገር እንዳልሰማ ሰው " ዳይኖሰር ስትል አስታወስከኝ! ለምን ዛሬ ኤድናሞል ሙቪ አናይም? አሪፍ የዳይኖሰር ሙቪ አላቸው" ብላ በሚያማምሩ አይኖቿ አየችኝ! ጀብዱየን ውሃ ቸለሰችበት! ቅር እንዳለኝ ወደኤድናሞል የሚወስደን ታክሲ ስንጠብቅ አስገራሚ ነገር ተፈጠረ .... በሬ! የፈረጠጠ በሬ መንገዱን እያመሰው ከፊት ለፊታችን መጣ ... በእርግጥ ነፍሴን ለማትረፍ ባደረኩት ሩጫ ከበሬው የበለጠ ብዙ ሰው እየገፋሁ ሳልጥል አልቀረሁም! ልጅቱ ጋር በተፈጠረው ግር ግር እንደተጠፋፋን ከዛ በኋላ አልተገናኘንም! በእርግጥ ትዝ ያለችኝም የሆነ ካፌ ገብቸ ሁለት ሊትሩን ውሃ ከጠጣሁ በኋላ ነው!

@wegoch
@wegoch
@paappii
"የተኛህበትን ሳታመላክተኝ
ስታዞረኝ አደርክ ስታንከራትተኝ።"
.
.
.
ሄዷል። ድንገት። ድንገቴው ለኔ ነው። የት እንደሄደ፣ ለምን እንደሄደ ምኑም አልገባኝም። ሳይገባኝ ልፈልገው ጣርኩ። እየኖረ እንዴት ይሄዳል ሰው? መኖርም መሄድም እንዴት በኩል አፍታ ይገለጣሉ? ባንድ ሰውነት ላይ እኩል? ስሄድ ጭልጥ፣ ግንጥል ብሎ መሄድን፤ ስኖር ጥግት፣ ጥብቅ ብዬ መኖርን ነው የማውቅና ግራ ገባኝ።

አስራ አምስት አመታት የጎነጎነው በሱ በኩል ለቆት ኖሮ ያለመልኩ ብትንትን፣ ጭብርር፣ ስብርብር አለ። ልብና አይምሮዬ ላይ አለ እና ሄደ ተደራረበ። እንኖራለን እያልኩ መኖርን ስሸምን መለያዬት ተከናነብኩ። ደህና መሆኔን፣ ሰላሜን፣ ቀጥና ቀና ብዬ መራመዴን የሄደ ቀን ይዞት ሄደ። ቀነጣጥሶኝ። እኔ እኔን አልሰማ አለች። አይቻት የማላውቃት ሌላ ሴትዮ ተፈለቀቀች። ያለመድኳትን ሴት ተሸከምኩ። የጎበጠች፣ አንገቷን የደፋች፣ ሰው የፈራች፣ ችላ ብትጠጋም የማትላተም። መውደድ የሚያስበረግጋት። መጠጋት እንዳያፍነከንካት በዛው አፍታ የመለየት ሃሳብ የሚያስፈራት ፈሪ ተፈጠረች።

መሄዱን ሂድ ግን እኔን መልስልኝ አልኩት የሆነ ቀን ሳወራው። ሌላ አላለም፣ ሙቭ ኦን እናድርግ ለሁለታችንም እሱ ነው የሚሻለን አለኝ። ቀድሞኝ ትቶኝ ተሻግሯል አውቃለሁ። እኔ ግን ወዴት እንደምሻገር ማወቅ ተሳነኝ። ድልድዬን ሰብረኸዋልኮ ልለው ነበር ይከፋዋል ብዬ ዝም አልኩ።

"እህህ ጠዋት ማታ እህህ ሌሊት
ይሄ ሆኗል ትርፌ ካንተ ያገኘሁት"
.
.
.
ሁሉም ይሄዳልኮ። መሄድ ሰውኛ ነው ማንም የሚሄደው። ልንሄድ ነው የመጣነው። የሚለዬው አካሄዱ ነው። የሄደው ሰው ዓይነት ነው። የቀረብን፣ ያጣነው ነገር ነው። ለዛ ነው የከበደኝ። ለዛ ነው እንዳዲስ ጉዳይ እያደር መሄዱን የማያምን ልቤ። ለዚሁ ነው እረሳሁት ባልኩ ማግስት ከሲናፍቀኝ ስሜት ጋር ግብ ግብ ገጥሜ ከራሴ የምጣላ።

ስነቃ ከሄደበት አፍታ መገረምና አለማመን ጋር እነቃለሁ። እውነት ሄዷል? በእህህታ ሳብሰለስል እውልና እንቅልፍ ዓይኔን ከመክደኑ ፊት በህቅታ እንዲወጣልኝ ከእንባዬ ጋር እንዳንገዋለልኩት ሽፋሽፍቴ እንደራሰ እንቅልፍ ይጥለኛል። ስነቃም ሃሳቤ ውስጥ ይኖራል። እንዲያ ሆነ የኑሮዬ ድግግሞሹ። በሆነ ባልሆነው ተነጫነጭኩ። ራሴ ላይ፣ ሃሳቤ ላይ፣ እቅዴ ላይ፣ ህልሜ ላይ፣ ቁጭቴ ላይ፣ ትላንቴ ላይ፣ ዛሬዬ ላይ፣ ነገዬ ላይ፣ ህይወት ላይ፣ እግዜሩ ላይ።

ለምን እንደሄደ፣ ለምን እንደበቃሁት፣ ባይለውም ለምን እንደጠላኝ እንዲገባኝ ስዳክር ስድስት አመታት ተሻገርኩ ከህመሜ ጋር። እሱ እንዳለውም ተሻግሯል። አስራአምስት አመት የቆዬ አብሮነታችንን እንደዋዛ ጥሎ፣ ከራሱ ጋር ከነፍሱ ጋር ይደልቃል፣ በዝምታ።

በነዚህ ሁሉ ጊዜያት ለምን ግን እለዋለሁ እግዜሩን። በአካል የተገለጠ ሰው ሲያምረኝ። የሚያወራኝ፣ ምኑንም ምኑንም የሚቀባጥርልኝ። ያለመስመር፣ ያለመጠንቀቅ ሁሉን። ሳቅ የሚወልድልኝ። ወሬ አልቆብንም ዝም ብለን የምንቆይ። ዝምታችንም የሚያወራ። እንደገና የምንቀጥል። እሱን የሚያስረሳኝ። ሰው በሰው ነው የሚረሳው ይሉ የለ? የምረሳበትንም ባይሆን የሚተካልኝን ሰው አምጣው እንጂ እያልኩ ንጭንጭ እግዜሩ ላይ። ከትላንቴ ተጣብቄ አረጀሁኮ፣ አዲስ ዛሬ ስጠኝ እንጂ ንትርክ። ለምን እኔ ማንም የሌለኝ? ለምን እኔ ፍቅሬን የተነጠኩ? ለምን እኔን ከሰው አጥንት አልፈለቀከኝም? ከሰው ግራ ጎን አልሸለቀከኝም? ናፍቀሽኛል መባል አያምረኝም? አውሪኝ ትንሽ አትሂጂ መባል አይጎበኘኝም? ለምን እኔ? መች ነው የኔ ወረፋ? መች ነው ልቤ የሚሞላ ዳግም?

"ስሄድ ስሄድ ውዬ ስሄድ ስሄድ ነጋ
ጅብ አይበላም ብዬ የናፋቂን ስጋ"
.
.
.
ዛሬ ሌሊት በጣም ናፈቅኸኝ። ሁሌም ነው የምትናፍቀኝ፣ ሄዷል በቃ ብዬ አልተውኩህም። ትቶኛል በቃ ብዬ አልተቀየምኩህም። ትናፍቀኛለህ። እያለህ እንደምናደርገው በእኩለ ሌሊት ንፋስ ስልክ ጎዳና ላይ እንራመድ ብዬ ወጣሁ። አብረኸኝ ነበርክ። እያወራኸኝ፣ እያሳቅኸኝ፣ ያቺን ምላስህን አውጥተህ ትልልቅ ዓይንህን ለማጥበብ የምትታገልባትን ፊትህን እያሳየኸኝ። እየተራመድን ትተኸኝ ሮጥክ ልይዝህ ተከተልኩህ። አጥሩ የፈረሰው ዮሴፍ ቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ ተከትዬ ዘልዬ ገባሁ።

" እስኪ እናንተ ተኙ እኔ ስራ አለብኝ
ግንብ እገነባለሁ ፍቅር ተንዶብኝ"
.
.
.
አቅፌህ ካሸለብኩበት የጎረነነ ድምጽ ቀሰቀሰኝ። 'የኔ እህት እባክሽ ትለከፊያለሽ በዚህ ሌሊት አትምጪ፣ ብርዱም አይቻልም' መቃብር የሚቆፍር ጎልማሳ ቁልቁል እየተመለከተኝ። አያውቅም ቤቴ አንተ እንደሆንክ። አያውቅም የተናደ ፍቅሬን እዚህ እየመጣሁ ልገነባ እንደምጥር። አያውቅም ማንም እንደሌለኝ። አያውቅም ልክፍቴ ወዳንተ መምጣት እንደሆነ። አያውቅም የሚሞቀኝ እዚህ እንደሆነ። አያውቅም ምንም። ናፍቀኸኛል......

@wegoch
@wegoch
@paappii

By Martha Haileyesus
ሰውዬው የአራዊት ማቆያ ፓርክ ሰርቶ እንደ አንበሳ: ነብር: ጅብ እና የመሳሰሉት አራዊትን አስገብቶ ለተመልካቾች ክፍት አደረገ

ፓርኩን ሊጎበኙ ለመጡ ሰዎች መግቢያ 300 ብር ጠየቀ: የሚገባ ጠፋ

መግቢያውን ቀንሶ 200 ብር አደረገ: አሁንም የሚገባ ሰው የለም

ተስፋ ያልቆየረጠው የፓርኩ ባለቤት መግቢያውን 50 ብር ቢያደርግም ማንም ከፍሎ የሚጎበኝ አላገኘም

በስተመጨረሻ መግቢያውን በነጻ ሲያደርገው ከፍለን አንጎበኝም ያሉት ሰዎች ሁሉ ፓርኩን ሞሉት

ይህንን የተመለከተው ሰውዬ አራዊቶቹን ከታጎሩበት ሳጥን ውስጥ በመፍታት የፓርኩን መውጫ 500 ብር አደረገው 😁

@wegoch
@wegoch
@paappii

By zemelak endrias
ወደ እዚህ ሃገር እንደመጣሁ : አብዛኛውን ጊዜ: እኔን የሚመስል መልክ ያላቸው ባህር ማዶ ረጅም ጊዜ የኖሩ ኢትዮጵያዊ ሰዎች : ሌላ ኢትዮጵያዊ ሲያዩ ፊታቸውን ወደ ሌላ አቅጣጫ ያዞራሉ ፣ ወይም :ይኮሳተራሉ ፣በጭራሽ ሰላም አይሉም። ይሄ መዘጋጋት : በጣም ግራ ያጋባኝ ነበር ።

"እኔ ግን እንደእነሱ አይደለሁም ። አዲስ መጤ ኢትዮጵያዊ : ስመለከት ሠላምታ መስጠት ፣ ቡና መጋበዝ አለብኝ። ደግሞም እኛ ኢትዪጵያዊያን መቀራረብ እንጂ መገለማመጥ አይኖርብንም!" ብዬ ለራሴ ቃልገባሁ።

ይህን ቃሌን ለማፅናትም ወደ ጓሮ ሄጄ ሣር በጠስኩ ። ይህን ቃል ብገባም በከተማችን ውስጥ አዲስ ኢትዮጵያዊ ስደተኛ ሳላይ ከረምኩ።
ታዲያ ዛሬ : ገበያ ውስጥ እንደ ድንገት : የእኔን ሃገር ሰው የሚመስል ትንሽም ግራ የተጋባ የሚመስል ሰው አየሁ። በከተማችን ውስጥ ኢትዮጵያዊ ማግኘት ብርቅ ስለሆነ ፈጠን ብዬ
"ሀበሻ ነህ?" ካልኩ በሁዋላ "ማለቴ ኢትዬጵያዊ ነህ ?" አልኩት ።
አየት አድርጎኝ " አዎ "
'መቼ መጣህ ?'
"ሶስት ወር ይሆነኛል "
"ውይ አዲስ ነህ "
"አንቺ ስንት አመት ሆነሽ "
"እም ዕድሜዬ ነው? እ ብዙ ነው :በየት መጣህ ?"
"በሊቢያ "
"አሃ! መንገድ እንዴት ነው ?!"

"ሰላም ነው "

(በቃ ?! ከዛ በሁላ ምንድነው ምለው ? )

"እሺ እና ሁሉ አማን?"

እሱ: ቲማቲም እየመረጠ :" አማን ነው።"

ወደ ቃሪያ መረጣ ገባ

"እንደው ቡና ልጋብዝህ ?"

"ቡና አልጠጣም እኮ ጨጓራዬ አያመመኝ ተውኩ"

"እና ያምሃሀላ "
"አዎ "
"አይ ጥሩ ነው "
"ምኑ ?"
"እንደው የሃገር ሰው ማግኘቴ ደስ ይላል"

"እም እሱስ አዎ "

"ሱዳንስ እንዴት ናት "

"ደህና ናት"

"ሊቢያስ?"

ዞር ትኩር ብሎ አየኝ እና
"ደህና ነው"

"ሜዲትራኒያን'ስ ሰላም ነው ?"

ብዬ ለራሴ ክው ብዬ ደነገጥኩ ። የተወራ አይመለስም እንጂ :ይህን ዓረፍተነገር :ብውጠው ደስ ባለኝ
ልጁ ግን ትዝብቱን ውጦ ዝም አላለም።

"የኔ እመቤት ! ከዚህ በላይ ቆሜ ባዳምጥሽ: አሳነባሪዎቹስ ደህና ናቸው ማለትሽ አይቀርም ።" ብሎ( ምን አይነቷ ናት?) በሚል እጁን አወናጭፎ የገበያ ጋሪውን እየገፋ ትቶኝ ሄደ።

By abeba birhanu

@wegoch
@wegoch
@paappii
የአይነስውሩ ማስታወሻ.
_______

መምህር አብርሀም እባላለሁ ከሰንዳፋ ወጣ ብላ በምትገኝ ሶኮሩ አንደኛ ደረጃ ትምህርትቤት ውስጥ የአማርኛ መምህር ነኝ. ሶኮሩ ገና በዳዴ እየሄደች ያለችና ነዋሪዎቿም  እንደማንኛውም ኢትዮጲያዊ ከእጅ ወደ አፍ በሆነ የእርሻ ስራ የሚኖሩባት የገጠር ከተማ ነች. የሶኮሩ ሰው #አደራ ተይልዬ ሴና. ብሎ በኦሮሚኛ አንደበት እንግዳን ሲቀበል አንጀት ያላውሳል. ትርጉሙም በተክልዬ ጎራበሉ እንደማለት ነው ትምህርት ቤቱ ያለበት ስፍራ ለአካልጉዳተኞች አስቸጋሪ ከመሆኑ በተጨማሪ በቂ የብሬል መፅሀፍት እንዲሁም የአይናማ ፅሁፎችን የሚያነብልኝ ሰው አለመኖሩ ስራዬን ፈታኝ ቢያደርገውም  እኔ ግን የዚህን የዋህ እና ገራገር ህዝብ ልጆች ሳስተምር ታላቅ የሆነ የመንፈስ እርካታ ይሰማኛል. በዚህች ቦታ የገበያ እንቅስቃሴው ደካማ በመሆኑ የሚያስፈልጉኝን ነገሮች ቅዳሜ ቅዳሜ ወደሰንዳፋ ሄጄ የመሸመት ልምድ አለኝ. ሰንዳፋ በፍጥነት እያደጉ ካሉ ከተሞች አንዷ ስትሆን ከ አዲሳበባ ቅርብ ርቀት ላይ መገኘቷ ለዚህ እድገቷ ትልቅ አስተዋፆ አለው. እንደተለመደው በአንደኛው ቅዳሜ ከሰንዳፋ እቃ ሸምቼ የተፈጥሮ ግዴታዬን ለመወጣት እንዲሁም የሆዴን አመፃ ለማስቆም የሰንዳፋ መናሀርያ ውስጥ በሚገኘው መፀዳጃ ቤት ለመጠቀም ስገባ የመፀዳጃ ቤቱ ጥበቃ በተለመደችው የከንፈር መጠጣ ተቀበለኝ. ይህች ከንፈር መጠጣ እንኳን ከዚህ ሰው አብረን ከምናስተምረው መምህራን ጭምር  አለፍ ሲልም ከነዋሪው ሳይቀር ስለምትደርሰኝ አይምሮዬ ኖርማል ከማድረጉ የተነሳ ሰላም የሚሉኝ ስለሚመስለኝ እግዚአብሄር ይመስገን ለማለት አስብና ተወዋለሁ. መፀዳጃ ቤት ውስጥ እንደ ደራሲ ስብሀት ገብረእግዚአብሄር አዲስ ሀሳብ ሳላመነጭ የባጥ የቆጡን ሳስብ የሆነ ሀሳብ መጣልኝ: ጋሽ ስብሀት ግን ድርሰቶቹ ትንሽ ወጣ ያሉት ሀሳቡ ሽንትቤት ውስጥ ስለሚመጣለት ይሆን እንዴ? እያልኩ ሳሰላስል ቶሎ እየወጣችሁ የሚለው  የመፀዳጃ ቤቱ ጥበቃ ሰላላ ድምፅ ከሀሳቤ መለሰኝ. ወትሮውንም እዛ መቆየት ማልወደው እኔ ሱሬዬን እያስተካከልኩ ሽንትቤት ውስጥ ከ 30 እስከ 40 ደቂቃ #ትመጪንደው የሚለውን የሚካኤል በላይነህን ሙዚቃ እየሰማ የሚቆየው ጓደኛዬ እና እንዲሁም አለምን የቀየሩ የሳይንስና የፍልስፍና ውጤቶች እዚህ ቦታላይ እንደተወጠኑ ማንበቤ ታወሰኝ. ከመፀዳጃ ቤቱ ወጥቼ  ከሆቴል እንደወጣ ሰው ሂሳብ ስንት ነው? ብዬ ጥበቃውን ጠየኩት ጥበቃውም በሀዘኔታ ድምፅ አምስት ብር ሲለኝ ኪሴ የቀረችውን አስር ብር አውጥቼ ሰጠሁትና መልስ መጠበቅ ጀመርኩ: ጥበቃውም አምስት የብር ሳንቲሞች እየሰጠኝ አይዞህ መንገድ ላይ ኪሽ ኪሽ እያረክ ለመሄድ ይጠቅምሀል ሲለኝ በድንጋጤ ሳንቲሞቹን ለቀኳቸውና የምለው ስለጠፋብኝ በደመነፍስ የምመራበት ኬኔን ዘርግቼ ሳወናጭፍ ጥበቃው ጎንበስ በማለቱ ኬኔ አየሩን ሰንጥቆ ወደኔው ተመለሰ. ይህን ሲከታተል የነበረ አንድ በድምፁ ስገምተው ወደ ሀምሳዎቹ መጀመሪያ ያለ ጎልማሳ መሀላችን በመግባት አረጋጋን ከዛም ጥበቃውን ገሰፀውና ሳንቲሞቹን ከመሬት ለቅሞ ሲሰጠኝ እኔ በበኩሌ አልቀበልም, ከተቀበልኩ ፈጣሪ አይቀበለኝ. ይልቁንስ ለሱ ስጠው ብዬ መልስ ሳልጠብቅ በጣም ተናድጄ ስለነበር በፍጥነት በመውጣት ሄድኩኝ. እናንተዬ ግን እስከመቼ ይሆን አንዳንድ ሰዎች ሁሉም አይነስውር ለማኝ የሚመስላቸው? በኔ በኩል ሚዲያላይ የሚቀርቡ አንዳንድ ፊልሞችና ድራማዎች አይነስውራንን ለማኝ አድርገው በመሳላቸው , በቂ የሆነ ግንዛቤ ባለድርሻ አካላት ባለመስጠታቸውና እንዲሁም ሁሉንም በአንድ የመፈረጅ ማህበራዊ በሽታ ጉልህ ድርሻ አላቸው ብዬ አስባለሁ. እንደመፍትሄም ባለድርሻ አካላት አስተማሪ በሆነ  ኪነጥበባዊ መንገድ የአይነስውራንን ውስጣዊ ብቃት ማሳየት ቢችሉ, መንግስትና መንግስታዊ  ያልሆኑ ድርጅቶች ተናበው ለይስሙላ ያልሆነና ለህብረተሰቡ በቂ ግንዛቤን የሚፈጥር ስራን በብቁ ባለሞያዎች ቢሰሩ, አይነስውራን ከትምህርት ጎን ለጎን ያላቸውን ሞያ ወይም ውስጣዊ ክህሎት አውጥተው ቢጠቀሙ, ለዚህም መምህራን አይነስውራን ተማሪዎችን ገና ከልጅነታቸው በውስጣቸው ያለውን ነገር እንዴት አውጥተው መጠቀም እንደሚችሉ ቢያግዟቸው ጥሩ ውጤት ያስገኛል  ብዬ አስባለሁ

By ጫላ መኮንን

@wegoch
@wegoch
@paappii
ጁዲ የፍሎሪዳ ነዋሪ ናት

ዘወትር ጠዋት ተነስታ እንደምታደርገው በባህር ዳርቻው ላይ እየተራመደች የባህሩ ወጀብ ወደ ዳር ያወጣቸውን የፕላስቲክ ኮዳዎችን እየሰበሰበች ሳለ አንድ የፕላስቲክ ኮዳ ትኩረቷን ሳበው

የፕላስቲኩ ኮዳ በውስጡ መልእክት ነበረው : ሁለት ባለ አንድ ዶላር የገንዘብ ኖቶች እና አመድ ከአንድ ጽሁፍ ጋር ኮዳው ውስጥ ተቀምጧል

መልእክቱ የሚያስረዳው ኮዳው ውስጥ ያለው አመድ ጎርደን የተባለ የ70 አመት ሰው ሲሆን መልእክቱን የጻፈችው ደግሞ ሚስቱ ናት

👇🏾

"ጎርደን በህይወት እያለ አለምን መዞር ይወድ ነበር: በዚህም የተነሳ ከሞተ በኃላ የአስክሬኑን አመድ በዚህ የውሃ ኮዳ አድርጌ ባህር ላይ ልኬዋለሁኝ:: ማንም ይህንን መልእክት ቢያገኝ እዚህ ውስጥ ባስቀመጥኩት ገንዘብ እና የስልክ ቁጥር ደውሎ ጎርደን የት እንደደረሰ ይንገረኝ" ይላል መልእክቱ

በዚህ ሁኔታ ይህንን የውሃ ኮዳ ያገኙት ሁሉ ከየት ተነስቶ የት እንደደረሰ የራሳቸውን መልእክት እያስቀመጡ እና ለሚስቱ እየደወሉ እየነገሯት ጎርደን ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መጏዙን ቀጠለ

ጁዲ ቴንሲ የምትገኘው የጎርደን ሚስት ጋር ደውላ ባለቤቷ ፍሎሪዳ እንደደረሰ እንዲህ ስትል ነገረቻት

👇🏾

“ጎርደን በሰላም ፍሎሪዳ ደርሷል :በሰላም ጉዞውን ቀጥሏል:: ጉዞው ደስተኛ እንዲሆንለት የውሃውን ኮዳ በውስኪ ጠርሙስ ቀይሬ ወደ ቀጣይ መዳረሻው ልኬዋለሁኝ😂አይዞሽ ስቀልድ ነው: ምናልባትም ርቆ የሚሄድ ከሆነ ገንዘብ እንዳያንሰው ተጨማሪ አንድ ዶላር ጠርሙሱ ውስጥ አድርጊያለሁኝ"

ጁዲ የዚያን ቀን ከሰአት በኃላ በባህር ዳርቻው የሚገኙ ሰዎችን እንዲሰባሰቡ አድርጋ ለጎርደን መታሰቢያ ፀሎት በማድረግ ነፍሱ ታስባ እንድትውል አደረገች

@wegoch
@wegoch
@paappii

By Zemelak endrias
የአይነስውሩ ገጠመኝ
_

ሰላም  ስሜ ግሩም ሲሆን ጀሞ በሚገኝ አንድ የመንግስት መስሪያቤት ውስጥ ከሰበታ እየተመላለስኩ እሰራለሁ. ሰበታ በተለያየ የኢንዱስትሪ ምርቶች በሚታወቁ ፋብሪካዎች እራሷን ያጠረች መለስተኛ የኢንዱስትሪ ከተማ ስትሆን ልክ እንደ ዳርዊኒያን ቲዮሪ እድገቷ ዘገምተኛ ነው. ሰበታ ላይ አይነስውር ሆኖ የቤት ኪራይ ከመፈለግ ሗይት ሀውስ ውስጥ ቁንጫ መፈለግ ይቀላል. አንዳንድ አከራዮችማ ገና የጊቢውን በር አንኳክተህ #የቤት ኪራይ አለ? ስትል አለ ይሉህና በር ከፍተው ገና እንዳዩህ መብረቅ የወረደባቸው ይመስል ያማትቡና ውይ ለናንተ አይሆንም ሽንትቤቱ እንዲህ ነው, ውሻው ምንትስ ነው እያሉ መልስ ሳይጠብቁ በሩን ይከረችሙብሀል. እኔም በሰው በሰው ባገኘሁት የቤት ኪራይ ውስጥ መኖር ከጀመርኩ ሁለት አመት ሞላኝ. ሁሌም ጠዋት አስራአንድ ሰኣት የመነሳት ልምድ ቢኖረኝም ቢሮ የምገባው ግን አርፍጄ ነው. በአንደኛው ማለዳ ተነስቼ በጣም የምወደውን የህንድ ክላሲካል ከፍቼ ለስራ መዘጋጀት ጀመርኩ: ቁርሴን በልቼ ጫማዬን ለማድረግ ማታ ያጠብኩት ካልሲዬን ካሰጣሁበት የጠረጴዛ እግር ላይ ሳነሳ ከውስጤ እስከዛሬ የማይጠፋው አንድ ተከስተ የሚባል ልጅ ያደረገው ነገር ታወሰኝ. ነገሩ እንዲህ ነው: የሆነ ቀን ተከስተ ደወለልኝ: ተከስተ ምላሱን ያዝ ስለሚያረገው ረ ከማለት ዘ ማለት ይቀናዋል. ገና ስልኩን ከማንሳቴ #ስማ ግዙሜ: ብቻዬን ስለሆንኩ እስኪ ቲሸዝትና ሹዛብ አጋዛኝ. ሲለኝ የዛሬን አያርገውና ያኔ ትንሽ ትንሽ አይ ስለነበረ ወድያው እሺታዬን ገለፅኩለትና ተገናኝተን ወደ ገበያ አመራን: የምንፈልገውን ነገር እንዳገኘን ዋጋ ከተስማማን በሗላ #በቃ ተከስተ ክፈልና እንሂድ: ስለው ተከስተ ጎንበስ አለና ጫማውን መነካካት ሲጀምር ነጋዴው ፈጠን ብሎ አ አይዞህ የጫማህ ማሰሪያ አልተፈታም: አለው. ተከስተ ሰውዬውን ችላ ብሎ ይባሱኑ እጁን ወደካልሲው ሰዶ የሆነ ነገር አውጥቶ ዘረጋውና ኢሄ ስንት ነው? ሲለኝ በሀፍረትና በመጠራጠር ዝም አልኩኝ: ይህን ያስተዋለው ነጋዴ እጁን ወደአፍንጫው እያስጠጋ አስር ብርነው .ሲለው ተከስተ በድጋሜ ከተአምረኛ ካልሲው ውስጥ የመቶ ብር ኖት አውጥቶ ይኸው መቶ ብዙን አገኘሁት ሲል ላየው ሰው የደቡብ አፍሪካን ዳይመንድ ያገኘ አትሌት ይመስል ነበር. ነጋዴው እንዳይተወው ብር ሆኖበት በመፀየፍ ሲቀበለው እኔ በበኩሌ የሀገሬን የብድር እዳ ብቻዬን የተሸከምኩት በሚመስል ሁኔታ አንገቴን ደፍቼ በልቤ ሁለተኛ ተከስተ የሚሉት ጓደኛ እያልኩ ተከስተን በወጉ መንገድ ሳልመራው የተመለስኩበት አሳፋሪ ገጠመኝ ነበር. ይህን እያሰላሰልኩ ጫማዬን ተጫማሁና ከቤት ወጥቼ ወደታክሲ ተራ መጣደፍ ጀመርኩ: የሰበታ እግረኛ መንገድ ለአይነስውራን አስቸጋሪ ነው በተለይ ዝናብ ከዘነበ ውሀ ስለሚቋጥር ከሱ ይልቅ የኮሪደሩን ጫፍ በመያዝ አስፓልት ላይ መሄድ ተመራጭ ነው. አንድ ወዳጄ ሲያጫውተኝ ይህ መንገድ እንዲስተካከልልን ለከተማው አስተዳደር ብናመለክትም #ይሄ እኔን አይመለከትም የኢትዮጲያ መንገዶች ባለስልጣንን አናግሩ ብሎ መልሶናል ብሎኝ ነበር. በዚህ አይነት የኢትዮጲያ መንገዶች ባለስልጣንን ብናናግር #መንገዱ የተሰራው በጣሊያን ወረራ ጊዜ ስለሆነ እስኪ ለጣሊያን ኢምባሲ አመልክቱ. ማለቱ አይቀርም እያልኩ የአስፓልቱን ጫፍ ይዤ ስጓዝ  አንዱ ሀብታም ካቆመው ሲኖትራክ ጋር በግንባሬ ተላተምኩ: ወድያው የሆነ መስታወት እጄ ላይ ሲወድቅ ታወቀኝና እንዴ የመኪናው መስታወት ተሰበረ ብዬ ሳስብ #አይዞህ ዋናው አንተ መትረፍህ ነው መነፅሩ ይገዛል. ብለው አንድ እናት ሲያፅናኑኝ የተሰበረው የኔ መነፅር እንጂ የመኪናው መስታወት አለመሆኑ ገባኝ. ማዘርም ቆይ ልጄ አብረን እንሻገር ሲሉኝ ከመቅፅበት ድምጿ የግንባሬን ህመም ያስረሳኝ ሽቶዋ ከሩቅ የሚጣራ ወጣት መጣችና ቆይ እኔ ላሻግረው ብላ በለስላሳ እጇ ይዛኝ እያሻገረቺኝ ወንድሜ ይቅር በለኝ ገና ከመኪናውጋር ሳትጋጭ እያየሁክ ነበረ ጥፋቱ የኔ ነው ብላ ማልቀስ ስትጀምር በድርጊቷ ብናደድም ድምጿ በፈጠረልኝ ቆንጆ ምስል ውብ አይኖቿ ሲደፈርሱ በውስጤ እየታየኝ አለቃቀሷ ሆዴን አላወሰው: እቅፍ አርገህ አባብላትና ስታለቅሺ ደሳልሺኝ የሚለውን የአብነት አጎናፍርን ዘፈን ዝፈንላት የሚል ስሜት እየወረረኝ አታስቢ ደናነኝ አልኳት: ከተሻገርን በሗላም እንባዋን እየጠረገች በናትክ ይቅር በለኝ ስትለኝ #አይዞሽ ተርፊያለሁ ለወደፊቱ ግን እንደዚህ አይነት ነገር ሲገጥምሽ ዝም ከማለት ይልቅ በቻልሽው መጠን ሰውን መርዳት ይልመድብሽ ስላት ሳግ ባፈነው ድምጿ እኔኮ ሳያችሁ ስለምታስፈሩኝ ነው ደሞም ሁለተኛ አይለምደኝም ስትል ሳቄን እየተቆጣጠርኩ እኛ አናስፈራም አንቺም እንደዚህ ያሰብሽው ባለማወቅ ይመስለኛል: እኛን ቀርበሽ በማየት ለኛ ያለሽን አመለካከት መቀየር ይኖርብሻል. ስላት ልክነክ ጓደኛዬ እናንተን እንዳልፈራና ለናንተ የልቦለድ መጽሃፍት በድምፅ አንብባላችሁ እንደምታውቅ ነግራኝ ነበረ: እኔም ካሁን በሗላ መጥፎ አመለካከቴን ለማስተካከል እጥራለሁ: እባክህን: ይቅር ካልከኝ ጓደኛሞች እንሁን? እያለችኝ ታክሲ ተራ ስለደረስን ስልክ ተለዋውጠን ተለያየን. እኔም ዛሬ ላጋጠመኝ ነገር ጥፋተኛው ማንይሆን እያልኩና የወጣቷን ግልፅ መሆን እያደነኩ ወደስራ ገባሁ.

By ጫላ መኮንን

@wegoch
@wegoch
@paappii
አንድ ሚኒስትር፣ ሚኒስትር ዴኤታ እና ዳይሬክተር ቁጭ ብለው ስለወሲብ የጦፈ ክርክር እያደረጉ ነው።

ሚኒስትሩ ወሲብ 60% ልፋት፣ 40% ደግሞ መዝናናት ነው የሚል አቋም ይዟል። ሚኒስትር ዴኤታው ደግሞ የለም ወሲብ 75% ልፋት፣ 25% ደግሞ መዝናናት ነው ብሎ ተከራከረ። ዳይሬክተሩ በበኩሉ ወሲብ 90% ልፋት፣ 10% ደግሞ መዝናናት ነው ብሎ እንደሚያምን ገልፆ ተከራከረ።

ክርክራቸው በጦፈበት ደቂቃ አንድ የበታች ፈፃሚ ሰራተኛ ቢሮውን አንኳኩቶ ብቅ አለ። ይሄኔ ዳይሬክተሩ "እንደውም እሱ ይፍረደን!" አለና ክርክራቸውን ነገሩት። በደንብ ከሰማቸው በኋላ "ይቅርታ አድርጉልኝና ወሲብ ምንም ልፋት የሌለበት 100% መዝናናት ነው!" አላቸው።

አለቆቹ በመገረም "እንዴት እንደዚያ አልክ??" አሉት። ጀለስም ፀጉሩን እያሻሸ እንዲህ ሲል መለሰላቸው . . .

"በጣም ቀላል ነው! ወሲብ ምንም ዓይነት ልፋት ቢኖረው ኖሮ እንደተለመደው እኔ እንድፈፅምላችሁ ታዙኝ ነበረ!" 😁

By Gemechu Merara fana

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሊቢያ ጥቂት ሳምንታት ቆይቻለሁ።
የመጀመሪያው እስር ቤት: ሚስራታ በመባል የሚታወቅ አካባቢ ነው። ሰምሳሪው ( የህገወጥ ኮብላዮች አዘዋዋሪው) የላከብን አሻጋሪ ሰውዬ : መንገድ ጠፍቶት ይሁን ታክቶት ባናውቅም: እንደ እስራኤላዊያን በረሃ ለበረሃ ሲያባዝነን ቆይቶ : ሊቢያ ድንበር ላይ :በታጣቂ አጋቾች በግል እስር ቤት እንድንገባ አደረገን። መቼስ ያንዳንድ ሰው ማሻገር አይጣል።

የግል እስር ቤቱ : ከበረሃ ግድምድም የሚገኙ :ችፍግ ችፍግ ያሉ ቤቶች እና የወላለቀ ጣራ የሚታይበት አካባቢ ሲሆን : ክምር ፍርስራሽ የተቆለለባቸው : በጀርባ ታሪካቸው ደህና ቤት እንደነበሩ የሚያሳብቁ : ፤አንዳንድ ቤቶች ደሞ አጠር ብለው በአራት ማዕዘን የተሰሩ ሳጥን መሰል የበረሃ ቤቶች ያሉበት ጭርታው የሚያስፈራ ፤ ከተማ ይሉት ገጠር ሰፈር ሊሉት መንደር :የሚያወዛግብ ሥፍራ ነበር።

ሚስራታ በሚገኘው : እስር ቤታችን : ግርግዳው በቦምብ የፈረሰ የሚመስል: በሩ ላይ ያለው ቁልፍ የማይሰራ እና ከስር ደግሞ ሰው የሚያሾልክ ክፍተት ነበረው ። እና እዚህ የግል እስር ቤት ውስጥ: እኔና አስራ አምስት የምንሆን: እስረኞች ፍጥጥ ብለን ቁጭ ብለናል።

አሳሪዎቻችን ከሰዓት በሁዋላ መጥተው ይጫወታሉ :ጨዋታ ማለት :- ተኩስ ይለማመዳሉ : ተለማምደው ሲሰለቻቸው : ጥያቄ ይጠይቁንና ይዝናናሉ ። ብዙዎቹ ስለ ሃዲስ ሆነ ቁርዓን ምናምን ዕውቀት የሌላቸው ናቸው ።
-
አንዱ የእኛ ሰው እዛው አቆይተውት እንደ አስተርጓሚ ይገለገሉበታል።

ይቀናናሉ አሉ <እከሌ ቤት ያለው ቦንብ !> እንትና ያለውን መትረየስ ብዛት > እንትና የጥይት ቱጃር ! እንኳን ለራሱ ለልጅ ልጅ ቢያወርሰው አያልቅበትም !> እየተባባሉ :-

አስተርጓሚው ይሄን መሰል ወሬያቸውን በቀስታ . ይተረጉምልናል ።

<የልብስ ቁንሳጥናቸው ውስጥ ራሱ ቦምብ ይደረድሩበታል > ይለናል። ሃብታም ሲሆኑ : እንግዳ ሲመጣ እያዞሩ የሚያስጎበኙት ዲሽቃ እና ሞርታር ግቢያቸው ውስጥ እንዲኖራቸው ያልማሉ ።

አንዳንዴ የሚሉን ነገር እሱም አይገባውም ።

እኛ ደሞ በሊቢያ ትሪፖሊ ወደብ ደርሰን ወደ አውሮፓ መሻገር እነልማለን።

እነሱ ደግሞ ዶላር ከፍለን በዚያ ዶላር ስናይፐር መግዛት ይመኛሉ።

ህልማችን ጨርሶ አይገናኝም ።

እኛ ስናያቸው የሆነ ባዙቃ ጭንቅላት ያላቸው ይመስለናል ። እነሱ ደሞ እኛን ሲያዩ ዶላር እንመስላቸዋለን ። እናም ነጋ ጠባ ይቆጥሩናል ።

አስተርጓሚውን የሚነግሩት ብዙ ጊዜ የተለመደ ነገር ነው : ተቆጠሩ፤ ውጡ፤ ተሰለፉ ፤ ደውሉ ፤ የሚሉ ትዕዛዞችን የነገሩት ከሆነ: ትዕዛዙን ያወርደዋል።

<<እንደምት--ባሉ ---ሉሉ - !>> ሲል ይጀምራል : ይሄንን ቃል ከእሱ ሌላ ሰው ሲጠቀምበት አልሰማሁም።

በታሰርን በሶስተኛው ቀናችን:ይሄው አስተርሚ

<እንደምትባባሉሉሉ -ሉሉ > ብሎ ጀመረ፤

በአንዴው በመደዳ ገርመመንና ፤:ያሸከሙትን ጠርሙሶች የያዘ የላስቲክ ቀረጢት እንዳንከረፈፈ : " እ እንደ --ም --ት --ባ' ሉሉሉ ----"

በዜማ ነው የሚነግረን ፤ አለ አይደል ድሮ ልጅ ሆነን ጎረቤት ቡና ጥሩ ስንባል በምንጨምርበት የቅላፄ ድምፅ --- "፣

" እማዬ እንዳ--ለችችችች ኑኑኑ ቡናና ጠ'ጡጡ- ጡ ""

እኛም አንገታችንን ስግግ አድርገን

" እ እእእ ? " እንላለን - በዝማሬ መልክ - ድምፃችንን አንድ የሚያረገው: ስጋታችን ነው : አለማመናችን ድምፃችንን በአንድ ቀልፆት : በአንድነት ያስጠይቀናል።

እ---እ ?

"<እንግዲህ እንደ ምት ባባሉሉሉ : አንድ አንድ ጠርሙስ እየወሰዳችሁ : አናታችሁ ላይ አድርጋችሁ አንድ በአንድ ቀስ እያላችሁ ወደ ውጪ ውጡ ---ጡጡ ጡ ----">

<ኧ >! አልኩ ሌሎች እንደ እኔ አዲስ የነበሩትም

አብረው<<እህ ?>" አሉ ።

ከረጢቱን ወደ ላይ እያነሳ

<"አዎ ለማታውቁ ነው እንጂ ላወቀው ብዙም አያስፈራም ፤ አልሞ ተኳሾሽ ናቸው እና ጠርሙሱን ነጥለው ነው የሚመቱት --->

<ማለት ? እ ? እንዴት ? > በጥያቄ እናጣድፈዋለን

<ማለትማ ጠርሙሱ አናታችሁ ላይ ታስቀምጣላችሁ :- ከእነሱ አንደኛው አነጣጥሮ ይቱኩሳል ። >

<እንዴ ? እንደ ዒላማ ልናገለግል? >

<እይ - ዒላማው እናንተ ሳትሆኑ ጠርሙሱ ነው ። >

<የት ተቀምጦ? >

<አናታችሁ ላይ ። > ብሎ ከረጢቱን ከፍቶ መሬት ላይ አስቀመጠው ።

ልንጨቃጨው ልንጮህበት ስንል አሳሪዎቹ እየተጯጯሁ ሲገቡ :- ለድግስ እንደተጠራ ተጋባዥ ጠርሙሴቹን በነፍስ ወከፍ ብድግ ብድግ እያደረግን ወሰድናቸው።

<ዉጡ> ተባልን

ወጣን

<እንደም ት ባ ሉ ሉ ሉ -->- አለ ያ መዘዘኛ አስተርጓሚ

<እእእእ- እእእ> አልን - ያው ስጋት ባጠመደው የህብረት ድምፅ

<ወደ ጎን በመስመር ተደርደሩና አናታችሁ ላይ ጠርሙሱን ጭናችሁ ቀጥ ብላችሁ ቁሙ -----ሙ>

<ከዛስስስስስ? > አልን በድጋሚ በህብረት ፍርሃት ባሰለለው ድምፅ

አስተርጓሚው ቀለል አድርጎ

<<እንደምትባሉሉሉ ሉ ሉ --- ጥሩ ተኳሾች ስለሆንን ጠርሙሱን ብቻ ነጥለን ስለምንመታው እንዳትነቃነቁ እና ዒላማችንን እንዳታስቱንንንን>>

ከዚህ በሁዋላ ነው በህይወቴ እያሳዘነ የሚያስቅ ገጠመኝ ያየሁት።

አንዱ እስረኛ እንደ አበደ ሰው ሆነ፤ ሌላው ደግሞ የሚጥል በሽታ እንዳለበት ሰው ተንፈራፍሮ አረፋ ደፈቀ፤ ሌላዋ ተደፍታ አሸዋ ነስንሳ ተማፀነች።

እኔ ደፈር ብዬ ወደ አስተርግሚው ጠጋ ብዬ

<መሃል ጭንቅላቴ ጠማማ እና አባጣ ጎርባጣ ስለሆነ ጠርሙሱን አናቴ ላይ ማስቀመጥ ስለማልችል ዒላማቸውን አስታቸዋለሁ > ስል ነገርኩት ።

ዛሬም ሻሽ ሳስር ትዝ የሚለኝ ነገር ይሄው ነው።

እርግጥ እውነት ነው ጭንቅላት ውስጡ አባጣ ጎርባጣ ነው አይደል።

< እና እንደምትባባሉሉሉ ---- -->

@wegoch
@wegoch
@paappii

By Abeba Birhanu
Forwarded from ግጥም ብቻ 📘 (Leul M.)
ሰላም እንዴት አላችሁ ሶስተኛ ስራዬ የሆነዉ "እየዳነ ሄደ" የተሰኘ የአጫጭር ልቦለድ ስብስብ መጽሐፌን አዘጋጅቼ የጨረስኩ ሲሆን በሚታወቀዉ የህትመት ዋጋ ችግርና ተያያዥ ጉዳዮች ምክንያት በቅድመ ክፍያ ለማሳተም አስቤያለሁ።

ገፅ :- 280
ዋጋ :- 450

መጽሐፉ ቢኖረን እንወዳለን ለምትሉ ለሕትመት ዝግጁ የሆነ መጽሐፍ ይዤ እየጠበቅኋችሁ ነው።
     

     CBE Account :- 1000394805924 ሶስና ሰይፉ

በቴሌ ብር 0933304772 

ከላካችሁ በኋላ screenshot ላኩልን

#ምግባር_ሲራጅ

@getem
@getem
ኒላ ዘ መንፈስ
(አሌክስ አብርሃም)

ፊደል አበደች! ያች የአገር ምልክት የነበረች ቆንጆ አበደች! ያች ድፍን የአገሩ ወንድ የሚመኛት ቆንጆ፣ እርሷ ካልሰራችበት ፊልም አናይም የተባለላት ውብ ወጣት ኢትዮጵያዊት ተዋናይ አበደች። መጀመሪያ ነገሩ እንደተራ ሐሜት ነበር የታየው፣ ቆይቶ ግን ብቻዋን ስታወራና ስትስቅ አንዳንዴም ልክ እጎኗ ሰው ያለ እስኪመስል እጇን እያወራጨች ስታወራ የሚያሳዩ በስልክ የተቀረፁ ቪዲዮዎች ሶሻል ሚዲያው ላይ በተደጋጋሚ ሲለቀቁ ህዝቡ ማበዷን አረጋገጠ አዘነም! በተለይ በአንዱ ቪዲዮ የልብስ መሸጫ ቡቲክ ውስጥ ገብታ አንድ ቀሚስ ይዛ የሆነች ሴት ጋር እያወራች ትታያለች «አንች ደግሞ ሁሉ ነገር አይጥምሽም ! እሽ አሁን ይሄ ምኑ ነው ያስጠላሽ ? ፈዘዘ? በቃ የግድ ቦግ ማለት አለበት?» እያለች! ባለሱቋ ግራ ተጋብታ ታያታለች፥ ምክንያቱም ማንም ሰው ከጎኗ አልነበረም።

አንዳንዶች ገንዘብ አሰባስበን ህክምና እናስገባት ሲሉ ሌሎች ፀበል ይሻላል የሚል አስተያየታቸውን ሰጡ። የሆነ ሆኖ ስመ ጥሯ ፣ቆንጆዋና ታዋቂዋ ተዋናይ ፊደል አድማሱ ማንም ምክንያቱን ባላወቀው ምክንያት አበደች።ይሄ ነገር የጀመራት «ሂውማን ሄር» የተባለውንና በዋና ገፀ ባህሪነት የተወነችበትን ፊልም ካስመረቀች ሁለት ቀን በኋላ መሆኑን ቤተሰቦቿ ሰይፉ ፋንታሁን ለተባለ የቴሌቪዥን ሾው አቅራቢ ተናግረዋል።

በስራዋ የቀኑ ሰዎች አስደግመውባት ነው የሚል ነገርም በሰፊው ይናፈሳል። እንደውም የአፍሪካ ፊልም ፌስቲቫል ላይ ለመሳተፍ በሚል ሰበብ በዚያ ሰሞን ናይጀሪያ ሄዳ የተመለሰችው ተዋናይት ሲፋን ግዛቸው ከዚህ ጉዳይ ጋር ተያይዞ ስሟ ተነስቷል። ስለምትቀናባት ፊደል ላይ የናይጀሪያ መተት አሰርታባታለች የሚሉ ውስጥ አዋቂዎች ተሰምተዋል። በእርግጥ ጥርጣሬውን ከፍ ያደረገው ሲፋን አብረዋት ወደናይጀሪያ የተጓዙ የፊልም ባለሙያዎች ከተመለሱ በኋላ ናይጀሪያ ለሶስት ቀናት ቆይታ መመለሷ ነበር። እርሷ ግን ታስተባብላለች« አንድ የናይጀሪኣ ልብስ አምራች መቀመጫሽ ስለሚያምር ልብስ አስተዋውቂልን ብሎኝ የስቱዲዮ ፎቶ ፕሮግራም ስለነበረኝ ነበር የቆየሁት » ስትል። ብዙዎች ታዲያ "ኡኡቴ ናይጀሪያ መቀመጫ ጠፍቶ? " እያሉ አሽሟጠጡ!

የሆነ ሆኖ ፊደል አበደች። በትክክል ምንድነው የሆነው? ከፊልም ምርቃቱ አንድ ሳምንት ቀደም ብሎ ውድ የእራት ልብስ ከምትሰራላት ዲዛየነር ጋር በአንድ የፋሽን ስቱዲዮ ተገናኝተው በእለቱ ስለምትለብሰው ልብስ እያወሩ ነበር። የመረጠችው ልብስ ቆንጆና ውበቷን የሚያጎላ ቢሆንም ልብሱ ጋር አብሮ የሚሄድ ረዥም ፀጉር አንደሚያስፈልግ ዲዛየነሯ ነገረቻት። ፊደል በተፈጥሮ ፀጉሯ አጠር ያለና ከርዳዳ ነው። ብዙ ካወጡ ካወረዱ በኋላ ዲዛየነሯ ታዋቂ «ሂውማን ሄር» አቅራቢ ወደሆነ ደንበኛዋ ደውላ የምትፈልገውን ፀጉር አይነት ነገረችው። ደንበኛዋ እየሳቀ «አሁን ከህንድ የገባ አስገራሚ ፀጉር አለ፣ ልክ እንዳልሽው ነው» ብሎ አበሰራት! ወዲያው እንድታየው በሰው ልኮላት ፊደል ሞከረችው። በእርግጥም ፀጉሩ ሲያዩት ልብ የሚያስደነግጥ፣ እንደድቅድቅ ጨለማ የጠቆረ ግን ደግሞ ብርሃን ሲያርፍበት የሚያንፀባርቅ ውብ ሂውማን ሄር ነበር። ብዛቱና ርዝመቱ ከምንም በላይ ሲንቀሳቀስ መዘናፈሉ ፊደልንም ዲዛየነሯንም አስደሰታቸው። ዋጋው ከተለመደው ወደድ ቢልም ፊደል ብዙ አላስጨነቃትም።

እንደተለመደው የፊልሙ ምርቃን ዜና ሚዲያውን ሞላው። ብዙዎች ተውበው በአዳራሹ ተውረገረጉ ከምንም በላይ ግን የፊደል ውበት በእለቱ የለበሰችው ልብስና ፀጉሯ ለወንዶች ፈተና ለሴቶችም ቅናት ሁኖ ዋለ። በተለይ ፀጉሯ በብዙዎች ተደነቀ! ፊደል በቀጣዩ ቀን ከታዋቂው ባለሃብት ገስጥ ጥጋቡ ጋር የእራት ቀጠሮ ነበራቸው። ከዛም በፊት አንድ ሁለት ጊዜ አብረው ወጥተዋል። አሁን የምትይዘው መኪናም ግማሸ ወጩ የተሸፈነው በእርሱ ሲሆን ግማሹን ግን ለፍታ ደክማ ባገኘችው የራሷ ገንዘብ የተገዛ ነው። ብዙዎች እንደሚያስቡት ገስጥን የቀረበችው ለብሩ ብላ አልነበረም። ፊደል እንደዛ አይነት ሴት አልነበረችም። ገስጥ እንደአንዳንድ ባለሃብቶች «ገንዘብ ካላ በሰማይ መንገድ አለ» የሚል ትዕቢተኛ ሰው አልነበረም። አርፎ መሬት ለመሬት የሚሄድ ጨዋ ሰው ነው። በእርግጥ ስራውም መሬት ነክ ነው። ትራክተር እና የእርሻ ማሽነሪዎች አስመጭ። ሰሊጥና ቡና ላኪ። ምንም እንኳን ባለትዳርና የአራት ልጆች አባት ቢሆንም ፍቅራቸውን ግን ማቆም አልቻሉም ነበር። ግንኙነታቸው ሚስጥር ነው ማንም አያውቅም።

እና የዛን ቀን ምሽት ፊደልና ገስጥ በውድ ሆቴል ራት በልተው ወደክፍላቸው ገቡ። ገስጥ በቲቪ እያያት ክፉኛ ሲመኛት አድሮ ስለነበርና የቀማመሱት ዋይን ምኞቱን ስላባባሰው ገና ከመግባታቸው ልብሷን አወላልቆ ራቁቷን አስቀራት! እንዲህ ርቃኗን ቁማ ሲያያት ሊያመልካት ምንም አይቀረውም! በውበቷ በወጣትነቷ ፈዘዘ። ከምንም በላይ ወገቧ ላይ የሚዘናፈለው ጥቁር ፀጉር እንደእሳት የሚነድ ከመሰለው ቀይ ሰውነቷ ጋር ሲያየው ቀልቡን አሳተው። በፍጥነት ልብሱን አወላልቆ ፊቷ ቆመ! ትንፋሻቸው ናረ . . . ክፍሉ በአንዳች ሙቀትና ስሜት ሊፈነዳ የደረሰ መሰለ! እየተስገበገበ ጠጋ ብሎ አቀፋትና እጁን ፀጉሯ ላይ ሲያሳርፍ ...

«አንተ እከካም እጅህን አንሳ » የሚል የተቆጣ የሴት ድምፅ አምባረቀ። ሁለቱም በድንጋጤ ወደበሩ ዞሩ፥ ማንም የለም! ሁለቱ ብቻ ናቸው። ተያዩ ድምፁ የፊደል አልነበረም። ግራ እንደተጋቡ ያው ድምፅ ቀጠለ « ምን ይመስላል . . . ከቦርጩ ቂ..ምነቱ ወንድ ልጅ እንዲህ ሲዝበጠበጥ ደስ አይልም » ገስጥ ግራ ገብቶት ክፍሉን ቃኘ . . . ፍራሹን አንስቶ አልጋው ስር ተመለከተ ወዲያ ወዲህ ተራወጠ ።
«ወደዛ አታፈንድድብኝ፥ ልብስህን ልበስ ምን ይንዘላዘልብኛል እዚህ ! አስቀያሚ . . . ደግሞ ምንድነው ቂ. . ህ እንዲህ የጠቆረው? እየተንፏቀክ ነው እንዴ የምትሄደው? ከመጥቆሩ መዥጎርጎሩ! ሐብታም አይደለህ ቅባት ክሬም ምናምን አትጠቀምም? የቅባት እህል እየሸጥክ አንተ አፈር መስለሀል! ይሄ ሁሉ ሃብት ያላወዛው ፎከታም ሰውነት ሂሂሂሂሂሂ ፤ ደግሞ ችኮላህ ! ትራክተር ነገር ነህ ...ተንደርድረህ ልታርሳት ነው ? አንች ደግሞ ምን ሁነሻል? እኩያሽን አትፈልጊም ? ወይስ ደደብ ነገር ነሽ?

«ማነሽ አንች?» አንች አለች ፊደል በፍርሃት ዙሪያዋን እያየች
« ምናባሽ ያገባሻል ? አሁን ይሄን ፎከታም ወደዛች ጋንጩር ሚስቱ ላኪና ወደቤታችን እንሂድ ደክሞኛል»
«ወደቤታችን? ወደማን ቤት ? » መልስ የለም። ፊደል በድንጋጤ ልብሷን ለባበሰች ! ገስጥም እንደዚያው! ሁለቱም ደንግጠው እጃቸው ይንቀጠቀጥ ነበር። ከመታጠቢያ ቤት እስከቦርሳዋ ያልፈተሹት ነገር አልነበረም። ማንም አልነበረም ማንም! ሁለቱ ብቻ።

ገስጥ ፊደልን ወደቤቷ ሊያደርሳት በውድ መኪናው በዝምታ ተቀመጥው እየተጓዙ ነበር። ያ አስፈሪ የሴት ድምፅ «ምን ይዘጋችኋል ሙዚቃ የለም? ምኖቹ አዚማሞች ናቸው በቡድሃ !» አለ። ገስጥ በድንጋጤ ፍሬን ሲይዝ ከኃላቸው በፍጥነት የሚከተል መኪና ጋር ለትንሽ ከመላተም ተረፉ።
«አንተ ደንባራ በስርዓት አትነዳም እንዴ ? ይሄ እርሻ ቦታህ የምትነዳው ትራክተር አይደለም ይዘኸን እንዳትሞት»

«አንች የውሻ ልጅ ማነሽ ?» አለ በቁጣ
«አንተ ደደብ እኔን ነው የውሻ ልጅ የምትለው? እንዲች ነኝና ኒላ! » ብላ ፎከረች
«ኒላ?» አሉ ፊደልና ገስጥ በአንድ አፍ ?
ፊደል እቤቷ ደርሳ ከገስጥ መኪና ስትወርድ ሁለቱም ከፍርሃታቸው ብዛት ደህና እደር ደህና እደሪ እንኳን አልተባባሉም!

እቤቷ እንደገባች በሯን በፍጥነት ዘጋችና በፍርሃት እየተንቀጠቀጠች ዙሪያዋን ማየት ጀመረች! ድንገት ሳታስበው እንባዋ ተዘረገፈ!
«ምን ያነፋርቅሻል? ደግሞ እንዳለ ላብ ላብ ሸተሻል ተነሸና ሻዎር ውሰጅ?» አላት ያ የሴት ድምፅ !
«እንዴ ቆይ ማነሽ ?» አለች በድንጋጤ ግድጋዳውን በጀርባዋ ተደግፋ እየተንቀጠቀጠች!
«አትፈሪ ! አናላ እባላለሁ ! ነፍሴን ይማረውና ጓደኞቸ ኒላ ነበር የሚሉኝ . . . ኒላ ልትይኝ ትችያለሽ አንችም! »
«እሽ ኒላ ምንድነሽ? የት ነሽ? ምንድነው የምትፈልጊው ?. . .»
«ኦ እኔ ሰው ነበርኩ እንዳንች . . . በእርግጥ አሁን መንፈስ ነኝ . . . ከሁለት ዓመት በፊት ህንድ ውስጥ ነው የሞትኩት . . .ሁለቱን ዓመት የት እንደነበርኩ እኔም አላውቅም! ይሄ አናትሽ ላይ ያደረግሽው ፀጉር የእኔ ነው! ልክ ፀጉሩን ሰውነትሽ ጋር ሲነካካ አንች ውስጥ ሁኘ ነቃሁ!
«እ?» አለች ፊደል በበለጠ ፍርሃት ፀጉሯን እየነካካች!
«አዎ ! ፍቅረኛየ ጋር በባቡር ስንጓዝ ነበር ባቡሩ ሃዲዱን ስቶ ያለቅነው! ለመጨረሻ ጊዜ ከአደጋው በፊት ፍቅረኛየ ይሄን ፀጉሬን በእጁ እያበጠረ በጣም እንደሚወደው እየነገረኝ ነበር። እንድንከባከበውም አደራ ብሎኛል! ፀጉሬን አመልከው ነበር። በጓደኞቸ በዘመድ አዝማዱ ሁሉ የተደነቀልኝ ፀጉር! ምን ዋጋ አለው... አንች እንዲህ በማይረባ ቅባትና በዚህ አቧራ አገርሽ አጎሳቆልሽው እንጅ ውብ ነበር። የሆነ ሁኖ ከዚህ በኋላ መንፈሴ በፀጉሬ በኩል አንች ውስጥ ገብቷል። ሰውነትሽ የጋራችን ስለሆነ ለብቻሽ አትወስኝም ።

«ነገውኑ ፀጉርሽን እፈተዋለሁ» አለች እየፈራች!
ለውጥ የለውም! መንፈሴ ውስጥሽ ነው ያለው ! ፀጉሬን እንደመጓጓዣ ውሰጅው ! መንፈሴ ተጭኖበት የመጣ መጓጓዣ! አገልግሎቱን ጨርሷል። እና ከዚህ በኋላ የማንም ፎከታም ጋር አትሄጅም ፍቅረኛችንን አብረን እንመርጣለን ፣ ምግባችንን ፣ ልብሳችንን ፣ አብረን እንበላለን አብረን እንዘንጣለን ፣ እና ደስ የሚለን ፍቅረኛ ካገኘን አብረን እን. . . ሂሂሂሂ!

ይቀጥላል!

@wegoch
@wegoch
@paappii
በጣም ዘግናኝ ነገር ማለት አንድ ቤተሰብ ውስጥ አባት ሲሞት ሐዘኑ ሳያንስ "አባቴ አባቴ" እያለ መቸና የት እንደተወለደ የማይታወቅ ግድንግድ ልጅ ከች ማለቱ! (ያኔ ሚስቶችን አለማየት ነው! አስከሬኑንን ሁሉ በጀበና ቢፈነክቱት ደስታቸው) ብዙ ወንዶች ድብቅ ናቸው! በኋላ ነው ጣጣቸው እየተጎተተ የሚመጣው!

እና ሰውየው ጨዋ ነበሩኮ(ሰባት አመት ተጠናንተው ሁሉ የታጋቡ) በሰፈሩ "ትዳርማ እንደሳቸው" የተባለላቸው...የሁለት ልጆች አባት! ከስራ ቤት ከቤት ስራ "ምነው ልጅ ጨመር ብታደርጉ ሀብት አላነሳችሁ" ሲባሉ "ምንድነው ልጅ ማብዛት ያሉትን በወጉ ማሳደግ ነው ዋናው " የሚሉ! እና ድንገት ሞቱ ... ልክ የቀብሩ ቀን ሶስት እግዜር ዲኤንኤ ውጤታቸውን በመልካቸው የፃፈባቸው ፣ ቁርጥ ሟቹን የመሰሉ ጠረንገሎ ጎረምሶች አባቴ አባቴ እያሉ ተግተልትለው አልመጡም!? ሚስትም ልጆችም ሐዘኑን እረስተው በድንጋጤ ታዛቢ ሆኑ" ይሄ ሁሉ ልጅ" እያሉ... ወዲያው አስከሬን ሊወጣ ሲል አዲሶቹ ልጆች" አሁን አይቀበርም አህህህህ" ብለው እያለቀሱ እየተናፈጡ ምናምን ከለከሉ ! ለምን ይባላሉ...
"አራት እህቶቻችን ከኋላ እየመጡ ነው እንጠብቃቸው"😄

@wegoch
@wegoch
@paappii

By alex abrham
ኒላ ዘ መንፈስ 2
(አሌክስ አብርሃም)

በክፍል አንድ ትረካችን አናላ ወይም በቁልምጫ ስሟ ኒላ የምትባል ህንዳዊት ሴት ከፍቅረኛዋ ጋር ይጓዙበት የነበረ የመንገደኞች ባቡር ሐዲዱን በመሳቱ ትሞታለች። ይች ሴት በዘመድና ወዳጆቿ ዘንድ የምትታወቀው በውብ ጥቁር ፀጉሯ ሲሆን እርሷም ለፀጉሯ ያላት ፍቅር እና እንክብካቤ የማምለክ ያህል ነበር። ምን ያደርጋል ያ አደጋ ነፍሷን ነጠቃት። ሰው ሟች ነው! ቆንጆም ሴት ትሁን ጀግና ወንድ ማንም ከዚህ ህግ አያልፍም። ይሁንና ኒላ ለራሷም ባልገባት ሁኔታ ከሁለት ዓመት በኋላ እዚች ምድር ላይ ያውም ኢትዮጵያ ፣ ያውም ፊደል የተባለች ታዋቂ ኢትዯጵያዊ የፊልም ተዋናይት ውስጥ መንፈስ ሁና ተከሰተች። ኒላ ራሷ እንደምትለው ለሁለት አመት የት እንደነበረች ምን እንደነበረች አታውቅም! የምታውቀው ነገር ተዋናይቷ የገዛችው «ሂውማን ሄር» የኒላ እንደነበርና ተዋናይቷ ፀጉር ጋር ሲነካካ ለሁለት ዓመት ሙት የነበረ ፀጉሯ ህይዎት እንደዘራ፣ ወዲያው በፀጉሩ በኩል ሙሉ መንፈስ ሁና ሰውነቷ ውስጥ እንደገባች ነው። ቀጣዩን እነሆ . . .
** * ****

የዛን ቀን ምሽት ፊደል መተኛት አልቻለችም! በፍርሃት አልጋዋ ላይ ተቀምጣ ሳታቋርጥ ውስጧ ተቀምጣ የምታወራውን ኒላ ግራ በመጋባት ታዳምጣለች።
«ተነሽ ገላችንን እንታጠብ፤ በላብ ጠረን ገደልሽኝኮ » አለች ኒላ! ፊደል አሁንም እያላባት ቢሆንም ምን ትሁን ምን ትፈልግ የማታውቃት እንግዳ ፊት ልብሷን ማውለቅ ፈራች! በቀስታ «የእኔ እህት ለምን ወደምትሄጅበት አትሄጅልኝም ? ፀጉርሽንም ውሰጅው አልፈልግም በጣም እያስጨነቅሽኝ ነው!» አለቻት!

« አንች የማይገባሽ ደደብ ሴት ነሽ ልበል? ነፍስሽን ከስጋሽ «ተለይተሽ ሂጅ» ማለት ትችያለሽ? ራሴን እንዳጠፋ እየጠየቅሽኝ ነው? በቃ ይሄ የአንች ሰውነት የእኔም ነው! ፈልጌሽ አልመጣሁም! ደህና ያረፈ ነፍሴን አምጥተሽ የቀሰቀሽው አንች ነሽ! እንዴት እንደገባሁም እንዴት እንደምሄድም አላውቅም ! ያለን አማራጭ ተከባብረን አብረን መኖር አለበለዚያ ተያይዘን ወደመቃብር መውረድ ነው! ይብላኝ እንጅ ላንች፣ መሞት እንደሆነ ለእኔ ብርቄ አይደለም. . . ይልቅ ተነሽ እንታጠብ እንዴት ነው ላብ በላብ የሆነው በቡድሃ! ለሞላ ሰውነት እዚች ውስጥ ታስቀምጠኝ! » አለች በቁጣ!

ፊደል እየተንቀጠቀጠች ወደሻወር ሄደች! ልብሷን በፍርሃት . . . በቀስታ አወላለቀች! የሻወሩን ውሃ በቀስታ ከፍታ ሙቀቱን በእጇ «ቸክ » ካደረገች ኋላ በደንብ የሞቀ ውሃ እስኪወርድ ሰውነቷን በእጇ ከልላ ዳር ላይ ቆመች! ጠባቡ ሻዎር በእንፋሎት መታፈን ሲጀምር በቀስታ ወደሚወርደው ውሃ ራመድ አለች!
«እንዴ ፀጉርሽን ሳትሸፍኝው ልትገቢ ባልሆነ?» አለች ኒላ ! በጩኸት!
«እረስቸው ነበር » ብላ ሮዝ ቀለም ያለውን የፀጉር መሸፈኛ የፕላስቲክ ቆብ አጠለቀች ! እና የቀኝ ትከሻዋን አስቀድማ ወደውሃው ገባች! ውሃው የፀጉር መሸፈኛው ላይ ሲያርፍ ዝናብ የቆርቆሮ ጣራ ላይ የሚፈጥረው አይነት ድምፅ ይፈጥራል! ወይም እንደዛ ይመስላታል ፊደል።
«ኡኡኡኡ አንች የማትረቢ ሴት አብደሻል? ወደዛ ውጭ ! » ብላ ጮኸች ኒላ! ጩኸቷ ጎረቤት ሁሉ ይሰማ ነበር!
«እንዴ ምን ሁነሻል? ታጠቢ አላልሽኝም እንዴ?» ብላ ዘላ ወጣች!
«እና ታጠቢ ማለት ተቀቀይ ነው?እንደዚህ በተፍለከለከ ውሃ የምትቀቀይው ድንች ነሽ? ለነገሩ ከአንች ድንች ይሻላል ከንቱ! በዚህ አይነትማ ፀጉሬን ከጥቅም ውጭ ነው የምታደርጊው. . . ቆይ ቆይ ለመሆኑ ተምረሻል? ወይስ ይሄን መቀመጫሽን እያገማደልሸ ብር የሚያሳይሽ ማንም እከካም ቦርጫም ባለትዳር ጋር መተኛት ብቻ ነው እውቀትሽ?»

« ለምን ስትናገሪ ስርዓት አይኖርሽም ? እኔ ሴት አዳሪ አይደለሁም፣ የተከበርኩ የፊልም ባለሙያ ነኝ! ለከት ይኑርሽ ! መንፈስ ሁኝ ፀጉር የራስሽ ጉዳይ ነው! . . . » ብላ ቱግ አለች ፊደል! እንባ እየተናነቃት!

«ሂሂሂሂሂሂ ! የተከበርኩ? ማነው የሚያከብርሽ? ሂሂሂሂ ያች ጓዝ ሚስቱ ስትደብረው ነው አንች ጋር እየመጣ የሚዝናናው ትራክተር የሆነ ሰውየ ?! ወይስ ያ ካሜራ ፊት እንደበቀቀን የሚጮህ ዳይሬክተር ተብየ? ስሙንማ ይዞታል!የታባቱ ተምሮ ነው ዳይሬክተር የሆነው? የዩ ቲዮብ ምሩቅ ወይስ "ዳይሬክተር" የዳቦ ስም መሰለው እናቱ የምታወጣለት? አንችም "ዳይሬክተር አወጣኝ" እያልሽ ቀሚስሽን ትነሰንሻለሽ! ልብሽ እብጥ ብሏል!

"እንዴዴዴ"

"የምን እንዴ ነው! ያም ቦርጫም እከካም በገንዘቡ ነው የገዛሽ ፤እንደትራክተር! ትራክተር እንኳን ያርሳል፣ አንች በጀርባሽ ተነጥፈሽ የሰው ባል አምሮት መወጫ ከመሆን ውጭ ምን ጥቅም አለሽ? ፊልም ትላለች እንዴ ? ቦሊውድን ያላየ! ሁለተኛ እንደዚህ ትጮኺብኝና አሳብጀ ልብስሽን አስጥየ ነው መሳቂያ የማደርግሽ! ከንቱ! ሸር . . ጣ! አሁን ውሃውን አቀዝቅዥው ! ዘንቧጣ! ደግሞ ራቁትሽን ሲያዩሽ ምንድነው የምትመስይው? ልብስ ነው ሰው ያስመሰለሽ! ከአምስት ዓመት በኋላ ማንም ዙሮ የማያይሽ ቆዳ ፊት ነው የምትሆኝው! ያ ሰሊጣምና ትራክተራም ራሱ እንዳላየ ነው የሚያልፍሽ »

ፊደል ተሳቀቀች! ማንም በሰውነቷ እንዲህ ዝቅ አድርጓት አያውቅም! አይቷት የማይንሰፈሰፍ ወንድ የለም! ቢሆንም መመላለስ አልፈለገችም! ሲጀመር ምን ጋር ነው የምትመላለሰው? ይችን ጉድ ፈራቻት፤ ይችን አስቀያሚ ሴት ክፉኛ ፈራቻት! እናም በትህትና « እኔኮ ቀዝቃዛ ውሃ ስለማልወድ ነው» አለች! ፍርሃት በተቀላቀለበት ሳግ የሚተናነቀው ድምፅ ! ይችን ፍጥረት ትሁን ቅዠት ምኗም መጋጨቱ ...! እንደውም ወደፖሊስ ጣቢያ ሂዳ ኡኡ ልትል አማራት!እዛው አሳድሩኝ ልትል ፈለገች፤ ፈራች በጣም ፈራች!

«ወደድሽ አልወደድሽ ግድ አይሰጠኝም! ሰውነቱ የጋራችን መስሎኝ! በሙቅ ውሃ የተቀቀለ አስቀያሚ ሰውነት ውስጥ ተቀምጨ መኖር የሚያስደስተኝ ይመስልሻል? ወጣት ነኝ ሳልሞት በፊት ገና ሃያ አራት ዓመቴ ነበር ! ግን ደደብ አልነበርኩም! ስለሙቅ ውሃ በኃላ አስረዳሻለሁ! አሁን ሙቀቱን ቀንሽው በይ ! ምናይነቷ ውስጥ ነው ያስቀመጠኝ ? ቆንጆ ብቻ ! » ተነጫነጨች! ፊደል ቀዝቃዛ ውሃውን ጨመረችው እና «አሁንስ?» አለቻት የማትታይ የማትታወቅ ሴት በራሷ ፍላጎት ላይ ፈቃድ መጠየቋ ደግሞ አበሳጫት!
«በእጅሽ ሞክሪዋ እኔ መንፈስ ነኝ! እጅ የለኝ እግር ፤በአንች እጅ ነው የማውቀው !» ፊደል እጇን ዘርግታ የሚወርደውን ውሃ ሞከረችው
«አሁንም ትኩስ ነው በደንብ ቀንሽው » ቀነሰችው «አሁን ይሻላል! »

ፊደል በጣም ከመፍራቷ ብዛት ውሃ ውስጥ ሁና ሁሉ ያልባት ነበር። «ይልቅ የገላ ሳሙናሽ ሸታው ደስ ሲል» ፊደል አልመለሰችም! ኒላ ወሬዋን አላቆመችም! « ኡፍፍ ሻዎር ስወስድ. . . ፍቅረኛየ ሮሃንን ነው የማስታውሰው ! በጣም የሚያምር አስተማሪ ነበር . . .እንደዛ ሰሊጣም ሽማግሌሽ እንዳታስቢው! እዛ እከካም ዳይሬክተር ተብየ ጋርም እንዳታወዳድሪው ! ወንዳወንድ ነበር. . . ጅኒየስ! ብዙ ሐሳብ ነበረን!ብዙ! " ጮክ ብላ ማንጎራጎር ጀመረች

የህንድ ተራሮች ግዝፈት
ሞገስህን አይሸፍኑም
ሙቀት ያለህ ስሜት ያለህ
ተራራ ነህ ውብ ተራራ
በአለት ማንነትህ ውስጥ
ፍቅር የሚንተገተግ
እንደ እሳተ ገሞራ ...
ፊደል ድንገት «ግን አማርኛ እንዴት ቻልሽ ?» አለቻት! ከጠየቀቻት በኋላ በመጠየቋ ተሳቀቀች!እንደሰው እውቅና መስጠትና ማናገር አልፈለገችም ነበር።
«አማርኛ ምንድነው?»
«እንዴ ይሄ የምታወሪበት ቋንቋ ነዋ»
«እኔ የማወራው ሂንዲ ነው፤ አንችም የምታወሪው የሚሰማኝ ጥርት ባለ ሂኒዲ ቋንቋ ነው! ሲጀመር ደግሞ እኔ አላወራም! ለማውራት ከንፈር ምላስ ያስፈልጋል. . . መንፈስ ነኝ ከንፈርም ምላስም የለኝም ! እኔ የማስበውን የአንች ከንፈርና ምላስ ነው የሚያወራው ! አእምሮሽ አድርገሽ እይኝ! አእምሮ አያወራም ያስባል ወደከንፈር ትዕዛዝ ይልካል! በሌላ አባባል መስተዋት ፊት ቁመሽ ስናወራ ብትመለከች የእኔንም የአንችንም ወሬ የሚናገረው የአንችው አፍ ነው! »
«እ?» አለች ፊደል የበለጠ ጭንቀት ውስጥ ገብታ! ነገሩ ሁሉ ተገለባበጠባት! የሻወሩን የብረት ድጋፍ ይዛ እንደመቆም አለች።

«በይ አሁን እንውጣ . . . ተዘፍዝፈሽ ልታድሪ ነው እንዴ?»
«ግን ለምንድነው ስድብ የምትወጅው? »
« ስድብ ? ትንሽ ቁጡ ነኝ ! በተለይ ድድብናን አልታገስም. . . ለመሆኑ የስሜ ትርጉም ምን ማለት እንደሆነ ይገባሻል? አናላ ነው ስሜ . . .አናላ ማለት እሳት ማለት ነው! እሳት! እኔ ላይ እንደእንጨት አትድረቂ ትቃጠያለሽ !! ገለባ አትሁኝ ትቃጠያለሽ! ከገለባ ሰዎች ጋር አትጠጊ ውስጥሽ ያለሁት እሳት ነኝ እበላቸዋለሁ! በተለይ ፀጉሬን ማንም ካለእኔ ፈቃድ ከነካ እንደላስቲክ ነው የማቀልጠው! እኔ አናላ ነኝ ፤ አናላ ዘ መንፈስ! ከዚህ በኋላ ይሄ ሰው የሚያጨበጭብለት ከንቱ ሰውነትሽ እንደክብሪት ቀፎ ነው ! ውስጥሽ እሳት የሆንኩ እኔ አለሁ! አብረን አመድ መሆን አልያም የምለውን እያደረግሽ መኖር ነው ምርጫሽ!

ይቀጥላል!

@wegoch
@wegoch
@paappii
ኒላ ዘ መንፈስ 3
(አሌክስ አብርሃም)

የመጀመሪያዎቹ ሳምንታት አስፈሪ እና ግራ አጋቢ ነበሩ ለፊደል፤ ከባድ ሆነውባት አለፉ! እንቅልፍ ማጣት ግራ መጋባት ...በየቀኑ ፍርሃቷ ቀስ በቀስ እየለቀቃት ቢሄድም መልመድ ያልቻለችው አንድ ነገር መታዘዝን ነበር። ውስጧ ተደላድላ የተቀመጠችው የተረገመች ኒላ ደግሞ ማዘዝ ነፍሷ ነው። መታዘዝ ነፍስ ስጋና መንፈስን ለአዛዢ ማስገዛት ነው! ፊደል ከልጅነቷ በነፃነት ያደገች ልጅ ናት።ከፍ ስትል ከተማሪ እስከአስተማሪ፣ ከመንደር ጎረምሳ እስከሚጠጓት ወንዶች ለውበቷ ተንበርክከው ስትጠራቸው አቤት ስትልካቸው ወዴት ባይ አሽከሮቿ ነበሩ! አሞጋሿ ብዙ ነበር! ዞር ስትል የሚያሟት ፊት ለፊት ይሽቆጠቆጡላታል።

ሌሎችን በአይን እይታ ብቻ ቁጭ ብድግ የምታደርጋቸው ፊደል ዛሬ ምንነቷ ለማይታወቅ መንፈስ በእሷ አባባል«ገረድ» ሁናለች። ለምሳሌ ፊደል በተፈጥሮ ውበቷም ይሁን በሽቅርቅር ፋሽን ተከታይነቷ ሊነኳት እንኳን የምታስፈራ ንፁህና ቆንጆ ትሁን እንጅ ቤት ውስጥ ዝርክርክ ነበረች። የበላችበት ዕቃ ለቀናት ሊከመር ልብሷ እዚህና እዛ ተዝረክርኮ ለሳምንታት ሊቆይ ይችላል። ኒላ ደግሞ ፈፅሞ ከዚህ ተቃራኒ ናት። አይደለምና መዝረክረክ ፊደል በራሷ ቤት ከነጫማዋ ምንጣፍ ላይ ከወጣች ታብዳለች!
«አንች የማትረቢ ቆሻሻ . . .» ብላ ነው የምትጀምረው!

አንድ ቀን ጧት (ሌሊት ማለት ይቀላል ከጧቱ አስር ሰዓት ) ፊደል በጥልቅ እንቅልፍ ውስጥ እንዳለች በሚያስበረግግ ጩኸት «ተነሽ» አለቻት ኒላ !ጩኸቱ ፊደልን አስበርግጎ ቀኑን ሙሉ ለእራስ ምታት ዳረጋት ! ቢሆንም ፊቷን እንዳጨፈገገች ተነስታ አልጋዋ ጫፍ ላይ ተቀመጠች!
«ዛሬ ይሄን ቤት እናፀዳለን»
«እንዴ . . .»
«አፍሽን ዝጊ ! እንደዚህ የተግማማ ቤት ውስጥ ልኖር አልችም! ገና ለገና መንፈስ ነኝ ታይፎይድና ታይፈስ አይዘኝም ብየ ዝም ልል አልችልም! ድብርት ራሱ ከታይፎይድ እኩል ነው! ቆሻሻ አልወድም ነገርኩሽ! ቆይ ለመሆኑ የምትኖሪው ለእነዚህ ተጎልተው የአንችን የማይረባ ፎቶና አርቲ ቡርቲ ፊልም ለሚያዩ ድንዙዞች ነው ወይስ ለራስሽ? ውጭ አፈር አይንካኝ ትያለሽ ቤትሽ ግን በክቷል ለራስሽ ክብር የለሽም ? በዚህ ቤት ነው እንግዳ የምንጋብዘው? »
«የምን እንግዳ ነው ! እኔ ማንንም እቤቴ አልጋብዝም. .»
«እኔ እጋብዛለኋ»
«ምን. . .?»
«እ ን ግ ዳ እጋብዛለሁ!!
«የምን እንግዳ ነው በቤቴ የምትጋብዥው ? አልበዛም?»
« ቤ ታ ች ን በይ!»

«አልልም ቤቴ ነው! »

«ቤታችን ነው» ፊደል ደከማት ! መንፈስ ግን አይደክመውም ይሆን ስትል አሰበች! የዛን ቀን ለዓመታት ያልተፀዳ ቤቷን ለማፅዳት ስትፈጋ ዋለች!ከኪችን እስከሸንት ቤት ከበረንዳ እስከግቢው ወገቧ እስኪንቀጠቀጥ አፀዳች! ኒላ ዘና ብላ ታዛታለች! ትሰድባታለች ልክ የባሪያ አሳዳሪ ነበር የምትመስለው! » ራሷን እስክትስት ቢደክማትም ውጤቱ ለራሷ ገረማት።

በዚህ ሁኔታ አንዴ ሲጣሉ ሌላ ጊዜ ሲኮራረፉ ቀናት ነጎዱ! ይች ግራ የገባት መንፈስ እንደባሪያ ያዘዝኩሽን አድርጊ ስትላት ያለመደችው መታዘዝ ከእልህ ጋር እየተቀላቀለ ግራ የገባት ልጅ አደረጋት! ቢሆንም ይች ወፈፌ ከታዘዘቻት የማትቆጣ እንደውም ትሁትና የጓደኝነት መንፈስ ያላት ፍጥረት መሆኗን ተረድታለች። አንዳንዴ ለቀናት ድምፅዋን ስለምታጠፋ ትታት የሄደች ይመስላት ነበር። ይሁንና ስሟን ጠርታ አለሽ ወይ ማለት ትፈራለች!አብረው በቆዩበት ጊዜ አንዳንድ ባህሪዎቿን ማወቅ ችላለች። እና በፀባይ ልትይዛትና እስከወዲያኛው የምትሸኝባትን መንገድ ለመፈለግ ወሰነች!

አንድ ቀን እንዲሁ ሲነታረኩ ውለው እንደተኮራረፉ ፊደል ለመጀመሪያ ጊዜ መንፈሷን በስሟ ጠራቻት
«ኒላ »
«ምን ፈለግሽ?»
«ይቅርታ ስላስቀየምኩሽ . . . ግራ ገብቶኝ ነው » ኒላ ዝም አለች! «እንደምታይው አድናቂ እንጅ ጓደኛም ዘመድም የለኝም! ብቸኛ ነኝ! የሚመጡት ሁሉ ወይ እውቅናየን አልያም ሴትቴን ፈልገው የሚመጡ ናቸው ጥልቅ ብቸኝነት ውስጥ የምኖር ብቸኛ ሴት ነኝ! እባክሽ ተረጅኝ»

« የነገርሽኝ ነገር አያሳዝንም. . .እዛ ሂጅና አብራሽ የምታለቃቅስ ሴት ፈልጊ! ልፍስፍስ ሴት አልወድም!ኢትዯጵያዊያን ተያይዘን እንውጣ ከሚላችሁ ይልቅ ሙሾ የሚያወርድላችሁን አስለቃሽ ነው የምትወዱት! አንች ራስሽ ራስሽን የምታደንቂው መስተዋት ፊትኮ ነው! የራስሽ እንኳን ጓደኛ አይደለሽም! ማንም የሚገዛሽ ለገበያ ያቀረብሽውን ነው! መቀመጫሽን ያቀረብሽለት አለም አዕምሮሽን ሊመርጥ አይችልም! ምኔን አይተው ተጠጉኝ ከማለትሽ በፊት ምንሽን አሳየሻቸው? ታዋቂ ነሽ እንጅ አያውቁሽም! ራስን ሸፍኖ እወቁኝ እያሉ ማልቀስ አለ እንዴ? ኪንኪ ፀጉርሽን እንኳን በእኔ ፀጉር ነው የሸፈንሸው! አየሽ የቤት ኪራይ ባልከፍልም በፀጉሬ የመጣልሽን በረከት ተካፋይ ነኝ! ሸበላ ወንድም ከመጣ ተካፋይ ነኝ ሂሂሂሂሂሂሂ! በነፃ አይደለም አንች ውስጥ የምኖረው ሰው ለእናት አገሩ እጁን እግሩን አይንና ሌላ አካሉን እንደሚሰጥ ፀጉሬን ሰጥቸሻለሁ፤ ፀጉር አካል ነው! አፍንጫሽ ላይ ያለው ዲኤን ኤ ፀጉርሽም ውስጥ አለ! ስለዚህ ጡረታ የምወጣው አንች ውስጥ ነው» ፊደል በዝምታ ስትሰማት ቆየች!

ኒላ ቀጠለች «ለመሆኑ ሶሻል ሚዲያው ላይ ስንት ተከታይ አለሽ?»
«ወደአንድ ሚሊየን. . .»አለች ፊደል!
«ለዚህ ሁሉ ተከታይሽ ምን ሰጠሽው? ፎቶ ፎቶ አሁንም ፎቶ . . . ፎቶሽ ምንሽን ያሳያል ? ቂ . . .ሽን ፣ ጡትሽን ፣ እግርሽን ፣ ጥፍርሽን . . . ጥፍራም! ባለፈው ፊልምሽን ልታስመርቂ ስትዘጋጅ ፀጉር ቤት ስንት ሰዓት ቆየሽ . . . አምስት ሰዓት ፣ ማሳጅ ቤት ሶስት ሰዓት ልብስ ስትለኪ ስታወልቂ አራት ሰዓታት ! ቢያንስ በየሳምንቱ «ራስን መጠበቅ» በሚል ሰበብ እድሜሽን መስተዋት ፊት እንደሽንኩርት በመላጥ የምታጠፊውን ጊዜ አስቢ! በዚህ መሃበረሰብ ውስጥ የአንች ቂ . . . ጤና ጣቢያ ነው ትምህርት ቤት? ቁንጅና ጥሩ ነው ! ግን ትንሽ ክፍተት ትንሽ መስኮት ነገር ከቁንጅናሽ አልፈው ወደአንች ሊገቡ ለሚፈልጉ ተይላቸው!

ድፍን ቆንጆ ብቻ አትሁኝ!በርና መስኮት የሌለው ደረጃ የሌለው ውብ ህንፃ ጥቅሙ ከውጭ መታየትና ለዙሪያው አዳማቂ መሆን ብቻ ነው!ሰዎች እንዲያርፉብሽ ውስጥሽ ትንሽ ወንበሮች ይኑሩ! እንደዛ ስልሽ እንደመሰል ጓደኞችሽ ነጠላሽን አደግድገሽ ለበዓል ካሜራ ፊት ድሆችን አሰልፈሽ ብሉልኝ ጠጡልኝ የምትይውን የሚያቅለሸልሽ «በጎ ስራ» አይደም! እሱ በጎ ስራ ሳይሆን «በጎ አድናቆት» ነው ! ምግብ መፀወትሽ እውቅናና አድናቆት ተመፀወትሽ! የለማኝ ሰልፍ ውስጥ ነሽ! ተደነቅሽበት ተወደሽበት ግን ባዶ ነሽ! ለራስሽ ስምና ዝና የምትቃርሚበት በጎ ስራ የስም ሜካፕ ነው! ራስሽን ብቻ ነው የሚያሳምረው! አንድ ቀን ሲዘንብ ታጥቦ አስቀያሚነትሽ ያገጣል!

«እስኪ ስለራስሽ ንገሪኝ » አለች ፊደል ትንሽ ጨዋታውን ለማስቀየር! ትችት አትወድም!

«ወሬኛ አትሁኝ ! እድሜ ልክሽን ስለሌሎች ሰምተሻል ፤አሁን ቢመርም ስለራስሽ መስሚያሽ ነው!. . .ለምንድነው ግን ኢትዯጵያዊያን አብዝታችሁ ስለሌሎች መስማት የምትወዱት? ራሳችሁን ትፀየፋላችሁ ወይስ በራሳችሁ ታፍራላችሁ?» ፊደል ዝም አለች! «ከድህነታችሁ በላይ አስከፊው ባህሪያችሁ ከእራሳችሁ መራቃችሁ ነው! ዙሪያችሁ ገደል እና ሚስጥር ነው . . .
ትዳር ይሁን ስልጣን ሐይማኖት ይሁን ማህበር ከነሸክማችሁ ስለምትገቡ እጣ ፋንታችሁ የሌሎችን ሸክም ማቅለል ሳይሆን ራሳችሁም ሸክም መሆን ነው። ራሳችሁ እንኳን ወደራሳችሁ የምትቀርቡበት አንድ ቀጭን መንገድ አድናቆት ብቻ ነው! ሰው በዚህ ልክ እንዴት ከራሱ ጋር ይጣላል በቡድሃ?!

ይቀጥላል!

@wegoch
@wegoch
@paappii
ኒላ ዘ መንፈስ 4
(አሌክስ አብርሃም)

በክፍል ሶስት ትረካችን ኢትዮጵያዊቷ ፊደል እና በሂውማን ሄር ሰበብ በውስጧ የገባችው ኒላ የተባለች የሙት መንፈስ (የፀጉሩ ባለቤት ነኝ የምትል) ከብዙ ስድድብና አለመግባባት በኋላ ቀስ በቀስ እርስ በእርስ ማውራት እንደጀመሩ፤ ፊደል ነገሩ በቁጣና በሐይል የማይሆን ስለመሰላት በውስጧ ተቀምጣ እንደ አለቃ የምታዛትን ነጭናጫዋን ኒላን በፀባይ ለመያዝ እንደወሰነች አይተናል። ይባስ ብሎ ኒላ ገና በቀናት እድሜ ስለፊደልና መሰሎቿ ኢትዮጵያዊያን ባህሪ እየጠቀሰች ፊደልን መምከርና መውቀስ ጀምራለች! ቆሻሻ እንደማትወድ በመግለፅ የፊደልን ቤት አስፀድታታለች! ኒላ መንፈስ ናት፤ ከሁለት ዓመት በፊት ህንድ ውስጥ በ24 ዓመቷ በባቡር አደጋ የሞተች ሴት መንፈስ! ከሞቷ በፊት እጅግ የምትወደውና የምትሳሳለት ፀጉሯ «ሂውማን ሄር» ተብሎ ወደኢትዯጵያ ተላከ ! ፊደል የተባለች ታዋቂ ተዋናይት ገዝታ ተጠቀመችበት፤ በዛው ቅፅበት የኒላ መንፈስ በፀጉሩ በኩል የፊደልን ሰውነት ተጋርቶ መኖር ጀመረ! አሁን ፊደል ማለት አንዲት ሴት ግን በውስጧ ሁለተኛ መንፈስ የሚኖርባት ግራ የተጋባች ሴት ሆናለች! ቀጣዩን እነሆ!

* * ** *

«አንች ህንዳዊ ነሽ ፣ እንደነገርሽኝ ኢትዮጵያን ካወቅሻት ገና የተወሰኑ ቀናት ቢሆንሽ ነው! ግን ስለእኔም ይሁን ሌሎች ኢትዮጵያዊያን ልክ እዚህ ተወልዶ እንዳደገ ሰው ትናገሪያለሽ ! የምትይውን ነገር ሁሉ እንዴት አወቅሽው? » አለች ፊደል የኒላን ቁጣና ዘለፋ የተቀላቀለበት ምክር በዝምታ ስታዳምጥ ከቆየች በኋላ!

«ስለመንፈስ ምንም አታውቂም? ይሄ የሚበዛው ክፍሉ በማይረባ ዝባዝንኬ የተሞላ አዕምሮሽ ለእኔ እንደኮምፒውተር ወይም እንደስልክ ነው አሰራሩ! መንፈስ ሁኘ ውስጥሽ ስገባ ከህፃንነትሽ ጀምሮ እስከአሁን የተጠራቀመ ትዝታሽ ችሎታሽ ፣ባህሪሽ፣ ስሜትሽ ሁሉም ነገር አንች የምታውቂውና የምታስታውሸው ሁሉ እኔ «ሜሞሪ» ላይ ተጭኗል። ግን የምጠቀመው የምፈልገውን ሲሆን የምጠቀመውም በእኔ በራሴ መንገድ ብቻ ነው! የራሴ ህልውና አለኝ ፣የራሴ አስተሳሰብና ስሜት አለኝ፣ የራሴ ችሎታና አረዳድ አለኝ፣ የሌለኝ አካል ብቻ ነው!

አካሌ እዛ ህንድ ተቃጥሎ አመዱ ወንዝ ላይ ተበትኗል! ከእንግዲህ እነዛ ውብ የሰውነት ክፍሎቸ ዳግም አይመለሱም! ያ ውብ ፈገግታየ የለም ፣ ስለዚህ ፈገግታሽን እጋራለሁ፣ እነዛ ውብ እግሮቸ እና እጆቸ የሉም ስለዚህ የአንችን እግርና እጅ እጋራለሁ ፣ ከንፈሮቸ የሉም የአንችን ከንፈሮች እጋራለሁ. . . ለዛ ነው እንደአሳማ የሚያገሳና እንደውሻ የሚናከስ ትንፋሹ ጋን ጋን የሚሸት ወንድ እንዲስምሽ የማልፈልው! ሁለታችንም ያልተስማማንበት ወንድ አጠገብሽ አይደርስም! ምክንያቱም ሰውነትሽ ሰውነቴ ነው! ሂሂሂሂሂ ስንት ነገር አለ! የተረፈኝ ብቸኛ መታሰቢያ ይሄ አንች አናት ላይ የተቀመጠው ፀጉሬ ብቻ ነው! ይሄ ፀጉር ሁሉ ነገሬ ምድር ላይ የቀረኝ ብቸኛ መታሰቢያ ነው። ጓደኞቸ የምወዳቸው ቤተሰቦቸና ነፍሴን የምሰጥለት ፍቅረኛየ ሁሉም ተረት ናቸው አሁን!ለዘላለም አብረውኝ አይኖሩም! ህይዎት እንዴት አጭር ናት? " አለች ባዘነ ድምፅ!

«ፀጉርሽ እንዴት ተረፈ ግን?»

በቤተሰቦቸ እምነት ሴት ልጅ በህይዎት ዘመኗ ሁለት ጊዜ ፀጉሯን ለምናመልክበት ቤተ መቅደስ ትሰጣለች፣ ልክ እንደስዕለት ነው! አንድ ከማግባቷ በፊት፣ ትዳሯ እንዲባረክ (ይሄ በፍላጎት የሚደረግ ነው) ሁለተኛው በወጣትነቷ ከሞተች! እንደገና ስትፈጠር በመልካም ሰው ወይም እንስሳ እንድትፈጠር! እኔ ግን አንች ውስጥ ተፈጠርኩ ሂሂሂ!

ምናልባት ያኔ ፀጉሬን ስቆረጥ ቅር ስላለኝ አምላካችን አዝኖብኝ ይሆናል። ልክ እናተ አስራት መባ ስጦታ እንደምትሉት ነው! በበሃላችን ፀጉር የመጨረሻው የሴት ልጅ ክብር አንዲት ሴት ለምታመልከው ጣኦት ፀጉሯን መስጠቷ ክብሯን ኩራትና ፀጋዋን ሁሉ ለአምላኳ የመስጠት ጥልቅ መንፈሳዊ ትርጉም አለው! ወይም ከቸገራት ፀጉሯን ሸጣ ኑሮዋን ልትደጉም ትችላለች! ማንም ሴት ቸግሯት ፀጉሯን ስትሸጥ ደስ ብሏት አትሄድም ከእንባ ጋር ነው!

«ቤተመቅደሱ ፀጉሩ ምን ያደርግለታል?» አለች ፊደል

ቤተመቅደሱ ፀጉሩን ሰብስቦ ሂውማን ሄር ለሚያዘጋጁ ካምፓኒዎች ይሸጠዋል ! ካምፓኒዎቹ አዘጋጅተው ወደመላው ዓለም ይሸጡታል! የእኔም ፀጉር በዚሁ መንገድ ነው የሚመጣው! እኔ የመጀመሪያውን ፀጉሬን በሰጠሁበት ቀን ስድስት ሺ ሴቶች ሰጥተዋል። ወደሁለት ቶን ፀጉር ማለት ነው! ሁለት መቶ ኩንታል ማለት ነው! ይሄ አንዲት ትንሽ ከተማ ላይ ብቻ ነው፤ በመላው ህንድደግሞ ብዙ ሚሊየን ኩንታል ይሆናል! አሁን የገረመኝ ከዛ ሁሉ ጉድ ፀጉር ስንት አገር እያለ እንዲህ አይነት ከአመት አመት ፀሐይና አቧራ የማይለየው፣ ዜጎቹም ግራ የተጋቡበት አገር መንቃቴ ! ይባስ ብሎ እንደአንች አይነት በዚህ ዕድሜዋ እንደ 11 ዓመት ልጅ የምታስብ ሴት ውስጥ መኖሬ . . .» አለች። ፊደል ፈገግ አለችና

«ግንኮ በዕድሜ እበልጥሻለሁ ለምን አታከብሪኝም ኒላ?»

«እሱማ አገራችሁም በዕድሜ ስንቱን አገር ትቀድማለች ? ግን አሁንም ገና ትላንት እንደተመሰረተ አገር እንደተወዛገበች እንደተደናበረች ነው! ጉራ ብቻ! ገና ጡጦ ላይ እኮናችሁ! የሶስት ሽ ዓመት ሚሚ ! » ፊደል ዝም አለች! አገር ጅኒ ጃንካ ይደክማታል።

ፊደል ቀኑን ሙሉ ከተማ ወጥታ ልብስና አስቤዛ ስትገዛ ውላ ተመለሰች! ኒላ ልብስ ታመራርጣት ነበር። በአንዳንድ ምርጫቸው ስለማይጋቡ መጨቃጨቃቸው አልቀረም! ፊደልን ከሩቅ የሚያይዋት ሰዎች «ለየላት» ይላሉ! በተቻላት መጠን ዝም ለማለት ብትሞክርም የኒላ ጭቅጭቅ ዝም የሚኣስብል አልነበረም። እንደውም በአንድ ቀሚስ ከለር ምርጫ ስላልተግባቡ ወደቤት ሲመለሱ ተኮራርፈው ነበር።


ፊደል ሻዎር ወስዳ ራት በልታ ወደምኝታዋ ስትሄድ ኒላ ድንገት ወሬ ጀመረች «እኔ የምልሽ ፊደል . . .ለምን የፌስ ቡክ አካውንት አትከፍችም ?»
"አለኝ ምን ያደርግልኛል! "

ለአንች ማን አለሽ ?

እና ለማን ነው ?

ለእኔ !

እንዴ ጭራሽ ?

ምን ችግር አለው? በስሜ ክፈችልኝ ጓደኞቸን አገሬን ቤተሰቦቸን ማየት እፈልጋለሁ! የድሮ አካውንቴን ባስብ ባስብ ማስታወስ አልቻልኩም! ይመስለኛል የእኔን ሜሞሪ ፕሮሰስ የሚያደርገው የአንች አዕምሮ ማስታወስ ላይ ትንሽ ደከም ያለ ነው መሰል ሂሂሂ !

እና ፌስቡክ አካውንት ያለው መንፈስ ልትሆኝ? አለች ፊደል ነቆራዋን እንዳልሰማ አልፋ! በነገሩ ግርምት ተፈጥሮባት ነበር።

አዎ! ክፈችልኝ! በዛውም የፍቅረኛየን የእኔን የድሮ የጓደኞቸን ፎቶ አሳይሻለሁ!

ፊደል ጉጉትና ፍርሃት ተቀላቀለባት ! ግን ጉጉቷ አሸነፋት! ይች ከሁለት አመት በፊት ሞትኩ የምትል ሴት ምን ትመስል ይሆን? እውነት ናት አንደሰው ምድር ላይ ኑራ ነበር? ጓጓች ! «ከፈለግሽ ምን ቸገረኝ» አለችና ወደማንበቢያ ጠረጴዛዋ ሄደች! ውስጧ ግን የሆነ የጅል ስራ እንደምትሰራ እየነገራት ነበር። ላፕቶፗን ከፈተችና «እሽ በምን ስም ልክፈትልሽ? »

ኒላ N I L A ፊደል ስሙን አስገባች ! ድንገት ግን ኒላ በሳቅ ፍርስ አለች ! ሂሂሂሂሂ ሂሂሂሂሂሂ ካካካካካኣ

ምን ያስቅሻል?
«ታይፕ አደራረግሽ ነዋ! ፊደሎቹን እያፈላለግሽ ነው የምትጫኝያቸው… አያቴ ነበር እንደዚህ የሚፅፈው . . . ይገርማልኮ አሁን አንች የተማርሽ ዘመናዊ ታዋቂ የፊልም ተዋናይ ነሽ! ታይፕ ማድረግ እንኳን በወጉ አትችይም! ይመስለኛል ታይፕ አደራረግ ወደፊት ማስተማር ሳይኖርብኝ አይቀርም!

ፊደል በስጨት አለች « አሁን የጀመርነውን እንጨርስ ወይስ ልተኛ ?» አለቻት በቁጣ !

«አትቆጭ ፊደል! ኢትዯጵያዊያን አለመቻላችሁ ሳይሆን አትችሉም መባላችሁ ያበሳጫችኋል! ቀኑን ሙሉ ስልክና ኮምፒውተር ላይ አቀርቅረሽ እየዋልሽ ታይፕ ማድረግ እንኳን በስርዓት አለመቻልሽ ሊያስቆጭሽ ነበርኮ የሚገባው!

ትልቅ እውቀት መሆኑ ነው? አለች ፊደል

ነውና! እኔ በአስራሁለት ዓመቴ ነው ጥንቅቅ አድርጌ ኪቦርድ አጠቃቀም የቻልኩት

«የራስሽ ጉዳይ ወሬ አለብሽ. . . በነገራችን ላይ እየረዳሁሽ መሆኑን አትርሽ »

«ሂሂሂሂሂ ሂጅ ካሜራ ማኖችሽን ጥሪና "ኒላን እየረዳኋት" ብለሽ ነገ ለአድናቂዎችሽ እዩልኝ በይ! . . . እሽ እያሳደድሽ የአባቴን ስም ፃፊ!

እንዲህ እያሉ ለኒላ አዲስ አካውንት ከፈቱ! በመጨረሻም ኒላ በምትነግራት መሰረት የኒላን ቤተሰቦች አካውንት ከፈቱ ! ኒላ መጀመሪያ ያየችው የወንድሟን አካውንት ነበር . . . እንደነፍሷ የምትወደውን ወንድሟን ! ፕሮፋይሉ ላይ «ውቧ እህቴን ካጣኋት ሁለት ዓመት ሆነ እንወድሻለን» ከሚል የእንግሊዝኛ ፅሁፍ ስር እጅግ ውብ የሆነች ሴት ፎቶ ይታያል!

ፊደል ልቧ ስንጥቅ አለ! ካሰበቻት በላይ ቆንጆ ሴት ነበረች ! ፀጉሯ በቀኝ ትከሸዋ በኩል አልፎ ፊት ለፊት እየተዘናፈለ ይወርድና ተፋዋ አካባቢ ድረስ ቁልቁል ወርዷል! ፈገግታዋ ሲበዛ ውብ ፊቷን የበለጠ አስውቦታል! የለበሰችው ደማቅ ቀይ የህንድ ባህላዊ ልብስ ድምቀቷን አጉልቶት ፎቶ ሳይሆን ህያው ስጋና ደም ያላት ፍጥረት አስመስሏታል!
«አንች ነሽ ? » አለች ፊደል ! ኒላ ግን ማልቀስ ጀምራ ነበር!
ፊደል በዝምታ ቆየች! ኒላ ለቅሶዋን አቁማ ሌላ ስም ነገረቻት! ፊደል ስሙን አስገብታ ስትከፍተው አንድ መልከመልካም ወጣት ከአንዲት ሴት ጋር በባህላዊ የሰርግ ልብስ አምሮ የሚታይበት የሰርግ ፎቶ ስክሪኑን ሞላው! ከጎኑ ቆንጆ ሚስቱ በፈገግታ ቁማለች!

ኒላ « ይሄ ቀልድ ወይም ህልም መሆን አለበት » አለች በቀስታ ! ከዚያም ድንገት «ውሻ የውሻ ልጅ » ብላ ጮኸች በጩኸቱ የፊደል ሰውነት ተናወጠ!
«ምንድነው ኒላ ?» አለች በፍርሃት ! «ፍቅረኛየ፣ ባቡር ላይ አብረን ሞትን ያልኩሽ ፍቅረኛየ ! ገና ከሞትኩ በሁለት ዓመቴ ጓደኛየን አግብቶ ነዋ! ይሄው አይታይሽም ይች ውሻ ጓደኛየ ናት . . . ጓደኛየ ! የራሴ ጓደኛ »

ፊደል ግራ ገባት « ቆይ ባቡሩ ላይ ሞተ አላልሽኝመረ . . .? »

«እኔጃ እኔ ስለሞትኩ የሞተ ነው የመሰለኝ ! አላውቅም . . . ምናልባትም ውሻ ቶሎ አይሞትም » ኒላ ዝም አለች ! ረዥም ዝምታ !

ኒላ አለች ፊደል የምታደረገው ግራ ገብቷት መልስ የለም . . . ኒላ ትሰሚኛለሽ ? ዝምታ ! በቀስታ ላፕቶፑን ዘግታ ወደምኝተዋ ሄደች! ዝምታው ያስፈራ ነበር።
ይቀጥላል!

@wegoch
@wegoch
@paappii
HTML Embed Code:
2024/04/19 11:25:27
Back to Top